AMN – የካቲት 22/ 2018
ኢትዮጵያና አዘርባጅን በእሴት ጨማሪ የግብርና መስኮች ላይ አብረው ለመስራት የሚችሉባቸው ጉዳዮች መፈተሻቸውን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት ፕሬስ ሴክሬታሪያት ኃላፊ ቢልለኔ ስዩም ገለጹ፡፡
የፕሬስ ሴክሬታሪያት ኃላፊዋ ቢልለኔ ስዩም የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአዘርባጃን ጉብኝትን በሚመለከት ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
በማብራሪያቸው በሁለቱ ሐገራት መካከል ትብብርን ለማሳደግ በሚያስችሉ ዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ሰፊ ውይይት መደረጉን የጠቀሱ ሲሆን፣ የግብርና ሴክተር ትብብሮችን ይበልጥ ማጠናከር አንደኛው ትኩረታቸው እንደነበር ጠቅሰዋል፡፡
ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በግብርናው ዘርፍ በተለይም በስንዴ ልማትና በሌማት ትሩፋት ያስመዘገበችውን ውጤትና ወደ አግሮ ፕሮሰሲንግ ለማሸጋገር ጥረት እያደረገች መሆኗን የጠቀሱት ብልለኔ ስዩም፣ መሪዎቹ ሁለቱ ሀገራ በእሴት ጨማሪ የግብርና መስኮች ላይ በጋራ ለመስራት የሚያስችሉዋቸውን ጉዳዮች መፈተሻቸውን ተናግረዋል፡፡
ከተፈረሙት የመግባቢያ ስምምነቶች አንዱ ግብርና ላይ ይበልጥ አብሮ ለመስራት መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
ኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል ላይ አቅም ያላት እንደመሆኗ ከአዘርባጃን ጋር ለመስራት ያሉ ዕድሎች መቃኘታቸውን ነው የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት ፕሬስ ሴክሬታሪያት ኃላፊ ቢልለኔ ስዩም ያብራሩት፡፡
የኢነርጂ መስኩን ይበልጥ ለማሳለጥ ለመተባበር መነጋገራቸውን ያነሱት ኃላፊዋ ፣ በጆይንት ኢንቨስትመንት አንድ ላይ መስራት የሚችሉባቸውን አማራጮች መመልከታቸውን ገልጸዋል፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ የተለያዩ የኢንዱስትሪ መስኮች እየተከፈቱ እንደመሆኑ እድሉም በጣም የሰመረና የሰፋ ስለሆነ፣ በኢንዱስትሪ በኩል አብረው ለመስራት ምን እድሎች አሉ የሚሉትን መወያየታቸውን አንስተዋል፡፡
በታደሰ ሽፈራው