የኢትዮጵያ የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት ሁሉም ዜጎች በእኩል የሚስተናገዱበት አካታች ስርዓት መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ኃላፊና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዓለምጸሀይ ጳውሎስ ገለጹ።
ከሰኔ 14/2017 ዓ.ም ጀምሮ ለሶስት ተከታታይ ቀናት “የሲቪል ሰርቪስ ተቋማትን ቅልጥፍና እና ጽናትን በማሳደግ በታሪክ አጋጣሚ የተፈጠሩ የአገልግሎት አሰጣጥ ክፍተቶችን መሙላት” በሚል መሪ ሃሳብ በአዲስ አበባ የተካሄደው 10ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመንግሥት አገልግሎትና አስተዳደር ፎረም ተጠናቋል።
የፎረሙ ማጠቃለያ መርሃ ግብርም የአፍሪካ ሕብረት፣ የአባል ሀገራት የስራ ኃላፊዎችና ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት ትናንት ምሽት በስካይ ላይት ሆቴል ተካሂዷል።
የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ኃላፊና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዓለምጸሀይ ጳውሎስ በዚሁ ወቅት፥ ኢትዮጵያ የህዝብ አገልግሎቶችን ለማሳለጥ ያከናወነቻቸውን ተግባራት በተሞክሮነት ስታጋራ ክብር ይሰማናል ብለዋል።
የዘንድሮው የአፍሪካ ሕብረት የመንግሥት አገልግሎትና አስተዳደር ፎረም የተሰጠው መሪ ቃል የተቋማትን የጋራ ርዕይ እውን ለማድረግ ትልቅ ምዕራፍ መሆኑን ገልጸዋል።
በአፍሪካ መዲና አዲስ አበባ የዓድዋ ድል መታሰቢያ፣ የብሔራዊ ቤተ-መንግስት ዕድሳት፣ የሳይንስ ሙዚየም ግንባታ፣ የከተሞች የኮሪደርና የቱሪዝም ልማት ፕሮጀክቶች እየተሳለጡ እንደሚገኝም አስረድተዋል።
የመሶብ አንድ ማዕከል የህዝብን የአገልግሎት ፍላጎት ያማከለና ሁሉም የዜጎችን በቴክኖሎጂ የተጋዘ፣ በአክብሮትና በኃላፊነት መንፈስ የሚገለገሉበት መሆኑን አስገንዝበዋል።
ኢትዮጵያ የተሟላ ማዕድ በሚወክለው የመሶብ አገልግሎት በሁሉም አካባቢዎች በማስፋት በዘመናዊ አገልግሎት የጋራ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ እየሰራች እንደምትገኝ ገልጸዋል።
የፎረሙ ተሳታፊዎች የመዲናዋ ጉብኝትም የአፍሪካ ህዝባዊ ተቋማት በአንድ ማዕከል ፍትሕዊና ዘመናዊ አገልግሎትን ለመሻሻል የተደረጉ ማሳያዎች መሆናቸውን ተናግረዋል።
የአፍሪካ የህዝብ አገልግሎት ቀን መካሄዱም በፍትሕዊነት፣ በዲጂታል ሥርዓት እንዲሁም ብቃት ባላቸው ሰዎች የሚመሩ ስኬታማ ተቋማትን ለመፍጠር ጉልህ ፋይዳ እንደሚኖረው ገልጸዋል።
የሕብረቱ አህጉራዊ የመንግሥት አገልግሎትና አስተዳደር ፎረም የዜጎችን ሁለንተናዊ ተቃሚነት ለማሻሻል የተደረጉ የፖሊሲ ለውጥ እርምጃዎችን ለማስቀጠል መጠቀም እንደሚያስፈልግም አስገንዝበዋል።
ኢትዮጵያም 10ኛው የአፍሪካ አህጉራዊ የህዝብ አገልግሎት ቀንን በማስተናገዷ ኩራት እንደሚሰማት መግለጻቸዉን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
በማጠቃለያ መርሃ ግብሩ ላይ በመንግስት አገልግሎታቸው ስኬት ያስመዘገቡ የኢትዮጵያ፣ የኬኒያ፣ የሴኔጋል፣ የደቡብ አፍሪካ፣ የዚምባቡዌ፣ የዛምቢያ እና የካሜሩን ተቋማትና የተቀማት የስራ ኃላፊዎች ዕውቅና ተሰጥቷቸዋል።