ጥራት ያለው የህክምና አገልግሎትን ለማስፋት በሁሉም አካባቢ የህክምና መሳሪያዎች ተደራሽነት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ ገለፁ።
ጤና ሚኒስቴር ከ4 ቢሊየን ብር በላይ ግምት ያላቸው የህክምና መሳሪያዎችን ለሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች አስረክቧል።
በርክክብ ስነ ስርዓቱ የተገኙት የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ እንደገለፁት፤ መንግስት የተሻለ የጤና አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ እያከናወነ ባለው ተግባር አበረታች ውጤት ተመዝግቧል።
ለዜጎች ጥራት ያለው የህክምና አገልግሎትን ለማስፋት የህክምና መሳሪያዎችን ማሟላት ትኩረት እንደተሰጠው መናገራቸውን ኢዜአ ዘግቧል።
በዚህ ረገድ የህክምና ተቋማትን ማስፋፋት፣ የህክምና መሳሪያዎችንና የመድሃኒት አቅርቦትን ማሟላት እንዲሁም የዘርፉን ሙያተኞች አቅም መገንባት ላይ በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል።
ዛሬ በኢትዮጵያ መድሃኒት አቅራቢ አገልግሎት በኩል ለሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች ተደራሽ የተደረገው የህክምና መሳሪያ የዚሁ አካል መሆኑን ጠቁመዋል።
ይህም የጤና አገልግሎትን ለማዘመንና ተደራሽ ለማድረግ ተጨማሪ አቅም እንደሚፈጥር ሚኒስትሯ ተናግረዋል።