የአሜሪካ ከፍተኛ ባለስልጣናት ከቻይና አቻዎቻቸው ጋር የንግድ ጦርነቱን ለማርገብ ተጨማሪ የንግድ ድርድር ለማካሄድ ለንደን ገብተዋል፡፡
የሳምንታት እድሜ ያለው የአሜሪካ እና ቻይና የንግድ ጦርነት እርቅ እየተሸረሸረ መምጣቱን ተከትሎ፣ ባሳለፍነው ሳምንት የሀገራቱ መሪዎች ለዛሬው የንግድ ድርድር ተቀጣጥረው ነበር፡፡
የአሜሪካ ልዑካን ቡድን በሀገሪቱ የገንዘብ ሚኒስትር ስኮት ቤሴንት የሚመራ ሲሆን፣ የቻናው ልዑካን ቡድን ደግሞ በቻይናው ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ሄ ሊፌንግ የሚመራ መሆኑን ስካይ ኒውስ ዘግቧል፡፡
ድርድሩ በሀገራቱ መካከል የነበረውን የንግድ ማዕቀብ ባስነሳው የጄኔቫው ድርድር ላይ የተነሱትን ሃሳቦች ያጠናክራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ያለፈው የጄኔቫ የንግድ ድርድር ለቀጣይ ድርድሮች አመቺ ይሆን ዘንድ በሀገራቱ መካከል የተፈጠረውን የንግድ ግለት ለማብረድ በሁለቱም ሀገራት መካከል ለ90 ቀናት ጊዜያዊ የከፍተኛ ታሪፍ ቅናሽ እንዲደረግ ማስቻሉ ይታወሳል፡፡