ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን ለአፍሪካ ዋንጫ በማለፉ የእንኳን ደስ አለን መልእክት አስተላልፈዋል፡፡
ይህ እግር ኳስ ወዳድ ለሆነው ህዝባችን ትልቅ የድል ብስራት ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን (ቀይ ቀበሮዎቹ) ኬንያን 3 ለ 0 በሆነ ውጤት በማሸነፍ ከ22 ዓመታት በኋላ ለአፍሪካ ዋንጫ በማለፋቸው እንኳን ደስ አለን ብለዋል፡፡
አቶ ተመስገን ጥሩነህ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸዉ ባሰፈሩት መልእክት በስፖርቱ ዘርፍ ታዳጊዎች ላይ በርትተን ከሰራን እግር ኳሳችን በአህጉራዊና በዓለም አቀፋዊ መድረኮች ከፍ የሚልበት ጊዜ ሩቅ እንደማይሆን ይህ ስኬት አመላካች ነው ብለዋል፡፡
የዛሬው ውጤት እንዲገኝ ሚናችሁን ለተወጣችሁ አካላት ሁሉ ምስጋናዬን እያቀረብሁ በድጋሚ እንኳን ደስ አላችሁ! እንኳን ደስ አለን! ብለዋል፡፡