ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ጉራፈርዳ ወረዳ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት እና ተጠሪ ተቋማት የተሰሩትን የሞዴል ገጠር ኮሪደር ስፍራዎችን ጎብኝተዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸዉ ባሰፈሩት መልእክት የገጠር ኮሪደር የአርሶ አደሮችን እና አርብቶ አደሮችን ሕይወት በመለወጥ ረገድ ትልቅ ሚና የሚጫወት ሀገራዊ ሥራ ነው።
ሞዴል ሥራው እያንዳንዳቸው ሳሎን፣ መኝታ ቤቶች፣ የእንስሳት ክፍል እና የውጭ መጸዳጃ ክፍሎች ያላቸው አስር ዘመናዊ ቤቶችን ያካተተ ነው። ቤቶቹ ከኤሌክትሪክ መስመር ጋር የተገናኙና የሳተላይት ዲሽ የተገጠመላቸው ናቸው። በተጨማሪም ጊቢው የዶሮ ማርቢያዎች፣ የእንስሳት በረት፣ የንብ ቀፎዎች ብሎም በፍራፍሬ እና አትክልት የተሞሉ ጓሮዎች አሉት።
የፀሐይ ኃይልን፣ ባዮጋዝ እና ሌሎች የልማት ሥራዎችን በመጠቀም ተቀናጅቶ የተተገበረው የገጠር ኮሪደር ልማት ሥራ ለማኅበረሰቡ ዘመናዊ፣ ጤናማ፣ ጽዱ እና ለተሻሻለ የአኗኗር ዘይቤ ጠንካራ እድል የሚሰጥ ነው። ይህ የለውጥ ሥራ በሁሉም ዘርፍ ረገድ እንዲስፋፋ ሁሉም የየድርሻውን ሊወጣ ይገባል ሲሉ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡