የ2026 ዓለም ዋንጫ ከተጀመረ ወዲህ የተሰሙ እና የታዩ አዳዲስና አስገራሚ ክስተቶች

AMN- ሰኔ 10/2018 ዓ.ም

በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በ48 ሀገራት መካከል የሚደረገውና በአሜሪካ ፣ ሜክሲኮ እና ካናዳ አስተናጋጅነት በደማቅ ሁኔታ እየተካሄደ የሚገኘው የ2026 ዓለም ዋንጫ ፣ ከተጀመረባቸው ጥቂት ቀናት ወዲህ በርካታ አዳዲስ፣ አስገራሚና አስቂኝ ክስተቶችን እያስተናገደ ይገኛል።

እስከ አሁን በውድድሩ ላይ የታዩና የተሰሙ ዋና ዋና ክስተቶች መካከል፡-

ታሪካዊው ባለሶስትዮሽ የመክፈቻ ሥነ-ስርዓት

በዓለም ዋንጫ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ውድድሩ የተጀመረው በአንድ ስታዲየም ሳይሆን በሶስቱም አስተናጋጅ ሀገራት በተዘጋጁ ሶስት የተለያዩ የመክፈቻ ሥነ-ስርዓቶች ነው።

እ.አ.አ ሰኔ 11 ቀን በሜክሲኮው ታሪካዊ ስታዲየም “ኤስታዲዮ አዝቴካ” የተጀመረው ደስታ፣ በማግስቱ በካናዳ ቶሮንቶ እና በአሜሪካ ሎስ አንጀለስ ስታዲየሞች በታዋቂ ድምፃውያን ትዕይንት ተከናውኗል።

በመክፈቻው ጨዋታ ብዙ የካርዶች መመዘዝ

የሜክሲኮ እና የደቡብ አፍሪካ የመክፈቻ ጨዋታ በሜክሲኮ 2 ለ 0 አሸናፊነት ቢጠናቀቅም ፣ በጨዋታው ላይ የታየው የካርዶች ብዛት ግን አስገራሚ ነበር።

በጨዋታው ላይ በአጠቃላይ 3 ቀይ ካርዶች የተመዘገቡ ሲሆን፣ ሁለቱ ለደቡብ አፍሪካ፣ ስፌፌሎ ሲቶሌ እና ቴምባ ዝዋኔ እንዲሁም አንዱ ለሜክሲኮው ተከላካይ ሴዛር ሞንቴስ ተሰጥተዋል። ይህ ክስተትም የመክፈቻ ጨዋታዎችን የጠበቀ ፉክክር ማሳያ ሆኗል።

ዳኞች ላይ የተገጠሙ ካሜራዎች

በማህበራዊ መገናኛ ብዙሃን ትልቅ መነጋገሪያ የሆነው የፊፋ አዲሱ የዳኞች ካሜራ ቴክኖሎጂ ነው። በመክፈቻው ጨዋታ ላይ ዋናው ዳኛ አንደርሰን ዳሮንኮ ላይ የተገጠሙት በርካታ ካሜራዎች ፣ ማይክራፎኖች እና የመገናኛ መሳሪያዎች መልካቸው ልክ እንደ ሳይንስ ልብወለድ ፊልም ገጸ-ባህሪያት እንዲመስሉ አድርጓቸዋል። ቴክኖሎጂው ለተመልካቾች አስገራሚ የሜዳ ላይ እይታዎችን እያሳየ ይገኛል።

የሜክሲኮ እና ደቡብ ኮሪያ ደጋፊዎች ወዳጅነት

በስታዲየሞች አካባቢ የታየው ሌላው አስገራሚ ክስተት የሜክሲኮ እና የደቡብ ኮሪያ ደጋፊዎች እያሳዩት ያለው ጥልቅ ወዳጅነት ነው። ይህ ታሪክ የሚጀምረው በ2018 ዓለም ዋንጫ ደቡብ ኮሪያ ጀርመንን በማሸነፍ ሜክሲኮ ወደ ቀጣዩ ዙር እንድታልፍ ከረዳችበት ጊዜ አንስቶ ሲሆን ፣ ዘንድሮም በሜክሲኮ ከተሞች የሁለቱ ሀገራት ደጋፊዎች አብረው ሲዘፍኑ፣ ምግብ ሲጋሩና ሲጨፍሩ የሚያሳዩ ተንቀሳቃሽ ምስሎች በስፋት ተሰራጭተዋል።

አስገራሚ የውጤት መደባለቆች

ውድድሩ ገና በምድብ ጨዋታዎች መጀመሪያ ላይ ቢሆንም፣ አንዳንድ ያልተጠበቁ ጠንካራ ፉክክሮች ታይተዋል፡፡

ጀርመን 7-1 ኩራሳኦ

የጀርመን ብሔራዊ ቡድን በኩራሳኦ ላይ ያሳየው የበላይነት እና የጎል ናዳ የውድድሩን ከፍተኛ ግብ የተስተናገደበት ሆኗል።

ቤልጂየም 1-1 ግብፅ

የግብፅ ብሔራዊ ቡድን ከጠንካራዋ ቤልጂየም ጋር ጨዋታ አድርጎ 1 ለ 1 በሆነ አቻ ውጤት ተለያይቷል።

ለመጀመሪያ ጊዜ 48 ሀገራትን የሚያሳትፈው ውድድሩ 104 ጨዋታዎችን የሚያስተናግድ በመሆኑ፣ ወደፊትም በርካታ አስገራሚ ክስተቶች እንደሚታዩበት ይጠበቃል።

በታምራት ቢሻው

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review