የአንድ ጀምበር ችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር፦
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ስምንተኛ ዓመቱን በያዘበት በዚህ ዓመት፤ የኮፕ32 (COP32) ሰብሳቢ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)፣ ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው እና የኮፕ32 ብሔራዊ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት በተገኙበት ዓመታዊውንና የአንድ ጀምበር ሀገር አቀፍ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብርን መርተዋል። ዘመቻው በመላው ሀገሪቱ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን በአንድ ቀን ውስጥ 800 ሚሊዮን ችግኞችን የመትከል ታላቅ ግብን የሰነቀ ሲሆን በዚህም ከተቀመጠው እቅድ በላይ ማሳካት የቻለ ዘመቻ ነበር። ይህ ጥረት በመላው ሀገሪቱ በሚገኙ ኢትዮጵያውያን የተከናወነ ሲሆን፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩም ተሳታፊዎች የታሪክ፣ የአንድነት እና የጽናት ድል ያስመዘገቡ መሆናቸውን በመግለጽ ለሁሉም ምስጋና አቅርበዋል።

ፕሮጀክቶች ጉብኝት እና ምረቃ፦
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በባሕር ዳር የሚገኘውን የደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ አዲስ ተርሚናል መርቀው ከፍተዋል። ይህ ፕሮጀክት ለኢትዮጵያ ቁልፍ ከሆኑ መግቢያ በሮች አንዱ መሆኑን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ከተማዋ በቅርቡ ባጋጠሟት ፈተናዎች ሳትበገር የጽናት፣ የማገገም እና የቀጣይ ኢንቨስትመንት ማዕከልነት ማረጋገጫ መሆኑን አስገንዝበዋል። አዲሱ ተርሚናል ዘመናዊ የአውሮፕላን ማረፊያ መሠረተ ልማቶችን፣ የተሻሻሉ የመዳረሻ መንገዶችን እና ሰፊ አገልግሎቶችን በማካተት የአውሮፕላን ማረፊያውን አቅም የሚያሰፋና የመንገደኞችን ምቾት የሚያሻሽል ሲሆን፤ ይህም ከከተማዋ ሰፊ የከተማ ትራንስፎርሜሽን ጋር ተዳምሮ ባሕር ዳርን ለዓለም አቀፍ እና ለሀገር ውስጥ በረራዎች ማዕከል ያደርጋታል።

ማኅበራዊ ጉዳይ፦
በሌላ በኩል ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከኦሮሚያ ብሮድካስቲንግ ኔትወርክ (OBN) ጋር ቃለ መጠይቅ ያደረጉ ሲሆን በቆይታቸውም ከሀገራዊ ጥቅም ይልቅ ግላዊ ጥቅምን ያስበለጡ በኦሮሚያ፣ በአማራ እና በትግራይ የሚንቀሳቀሱ የታጠቁ ቡድኖች መንግሥትን ለብቻቸው ማሸነፍ እንደማይችሉ ከተገነዘቡ በኋላ ህብረት መፍጠራቸውን ገልጸዋል።
በተጨማሪም ጊዜው ባለፈበት የፖለቲካ አስተሳሰብ እና የአመራር ዘይቤ እነዚህ ቡድኖች ኢትዮጵያን ለማዳከም እና ለመበታተን ለሚፈልጉ ታሪካዊ የውጭ ጠላቶች እንደ መጠቀሚያ መሣሪያ እያገለገሉ የመሆናቸውን ታሪካዊ ግድፈት አብራርተዋል።
አክለውም እውነተኛ ዲሞክራሲ ከተራ የፖለቲካ ግልጽነት ባለፈ የሕግ የበላይነትን ወደሚያረጋግጥ እውነተኛ ብሔራዊ ውይይት መሸጋገር እንዳለበት አፅንዖት ሰጥተዋል።