AMN—ሀምሌ 1/2018 ዓ.ም

ሀገር የምትገነባው በትውልድ በመሆኑ፣ ታዳጊ ተማሪዎች ውብና ለምለም ሀገርን ለመረከብ ዛሬውኑ ችግኞችን የመትከልና የመንከባከብ ልምድን ሊያዳብሩ እንደሚገባ የአዲስ አበባ ከተማ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዘላለም ሙላቱ (ዶ/ር) ገለጹ።

የአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ አመራሮች፣ ሠራተኞችና ባለድርሻ አካላት ጎሮ አካባቢ ችግኝ ተክለዋል።
”ተስፋን እንትከል” በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ በሚገኘው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ 20 ሺህ ችግኞችን በመትከል የድርሻውን እየተወጣ መሆኑን ገልጿል።

የቢሮው ኃላፊው ዘላለም ሙላቱ (ዶ/ር) የችግኝ ተከላ መርሃ ግብሩን ሲያስጀምሩ እንደተናገሩት፣ ሀገር የምትሠራው በትውልድ ስለሆነ ታዳጊ ተማሪዎች ያማረች ለምለም ሀገርን ለመረከብ ችግኞችን መትከልና መንከባከብን መለማመድ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡

የቦሌ ክፍለ ከተማ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ አደፍርስ ኮራ በበኩላቸው በክፍለ ከተማው ዘንድሮ 1.8 ሚሊዮን ችግኞችን ለመትከል ታቅዶ እየተተገበረ መሆኑን አስታውቀዋል።

በችግኝ ተከላው ላይ ከቦሌ እና ከለሚኩራ ክፍለ ከተሞች የመጡ መምህራንና ተማሪዎች እንዲሁም ከሁሉም ክፍለ ከተማ በርካታ ቁጥር ያላቸው ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
አረንጓዴ አሻራን ማኖር ልምላሜን ማስቀጠልና ሀገርን ማሻገር በመሆኑ እኛም ችግኞችን በመትከልና በመንከባከብ የዜግነት ድርሻችንን እንወጣለን ሲሉም ነው ተሳታፊዎች የገለጹት።
አዲስ አበባ ከተማ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር 6 ሚሊዮን ችግኞችን የመትከል ግብን ለማሳካት እየሰራች ትገኛለች፡፡
በምትኩ ተሾመ