AMN – መጋቢት 12/2017
በሚቀጥሉት አስር ቀናት የበልግ እርጥበት ተጠቃሚ በሆኑት ተፋሰሶች ከመጠነኛ እስከ ከፍተኛ እርጥበት ያገኛሉ ሲል የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ።
ይህም ሁኔታ የገጸ ምድር የውሃ ፍሰትን ስለሚጨምር ወደ ተለያዩ የውኃ ማጠራቀሚያዎች ውስጥ የሚገባውን የውኃ መጠን ከመጨመር አንጻር አዎንታዊ ጎን እንደሚኖረውም ገልጿል።
በአንጻሩ ግን ለጎርፍ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች ላይ ቅጽበታዊ ጎርፍ ሊያስከትል እንደሚችልም ኢንስቲትዩቱ አሳስቧል።
የጎርፍ ተጋላጭ አካባቢዎች ላይ የጎርፍ ፍሳሽ ማፋሰሻ ቦዮችን በማፅዳት ሊከሰት የሚችለውን ተጽዕኖ ለመከላከል ከወዲሁ የቅድመ ዝግጅት ስራዎችን ማከናወን እንደሚያስፈልግ ኢንስቲትዩቱ በማህበራዊ ትስስር ገጹ ያወጣው መረጃ ያመለክታል።