በኦሮሚያ ክልል ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሰዎች የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና መዉሰዳቸዉን የኦሮሚያ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ባለስልጣን አስታወቀ፡፡
የኦሮሚያ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ መኮንን በየነ ፣ በክልሉ 580 ሺህ የመንግስት ሰራተኞች፣ 190 ሺህ ተማሪዎች፣መምህራን እና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች በድምሩ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሰልጥነው የምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን ጠቁመዋል።
የስልጣናዉ ዋና አላማ ወጣቶችን በማብቃት በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት የስራ ዕድል እንዲያገኙ ለማስቻል እንደሆነ ዋና ዳይሬክተሩ አስረድተው፣ ኢንቨስትመንትን ወደ ሀገር ውስጥ ለመሳብና ለወጣቶች አቅም ግንባታ እንደሚያግዝ ገልጸዋል።

በአለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሆነና በቴክኖሎጂ የበለጸገ ትዉልድ ከመገንባት ረገድም ስልጠናዉ ትልቅ ጠቀሜታ ይኖረዋል ብለዋል ፡፡
በክልሉ የመንግስት አገልግሎትን ዲጂታላይዝ በማድረግ ቀልጣፋ፣ ጥራት ያለውና ከወረቀት ንክኪ ነፃ የሆነ አገልግሎት ለመስጠት እየተሰራ መሆኑን የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ፣ 123 አገልግሎቶችን በኢንተርኔት (online) ለመስጠት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ይህ አሰራር ከአንድ አመት ከስድስት ወር በኃላ በ23 ከተሞችና በ2 ዞኖች እንደሚተገበር ገልጸዋል።
ኦሮሚያን ዲጂታላይዝ የማድረግና የመንግስት አገልግሎትን እስከ ቀበሌ የማድረስ ስራ እየተሰራ በመሆኑ፣ ተገልጋዩም በቴክኖሎጂ ራሱን ማላመድና ማብቃት እንደሚገባቸው አሳስበዋል፡፡
በክልሉ 5 ከተሞች የተጀመረው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትም የኦሮሚያ ዲጂታል ስትራቴጂ 2030 ትግበራ አካል መሆኑንም ጨምረዉ አብራርተዋል፡፡
አዲስ እና ትልቅ የዳታ ማዕከል (Data Center) በክልሉ ለመገንባት ግንባታውን የሚያከናውን ኢንተርፕራይዝ መመስረቱንም መናገራቸዉንም የኦሮሚያ ኮሚኒኬሽን ቢሮ ለኤኤምኤን የላከዉ መረጃ ያመላክታል፡፡