AMN ጥር 27/2018
ታዋቂው የገዳ ሥርዓት ተመራማሪ ፕሮፌሰር አስመሮም ለገሰ ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸው ተሰማ። ፕሮፌሰር አስመሮም ለገሰ የተለያዩ የምርምር ሥራዎችን በየጊዜው ይፋ ሲያደርጉ የቆዩና በገዳ ሥርዓት ላይ ያተኮሩ መጻሕፍትን ሲያዘጋጁ የነበሩ ምሁር ነበሩ።
የገዳ ሥርዓት እንዲጠበቅ ከማድረግ ረገድ ትልቅ ሚና የተጫወቱት ፕሮፌሰር አስመሮም፤ ሙሉ ሕይወታቸውን የገዳ ሥርዓት እንዲታወቅና እንዲከበር፣ የሥርዓቱንም ፍልስፍና በጽሑፍ በማስፈር ሲተጉ እንደነበር ታሪካቸው ያስረዳል።
ፕሮፌሰር አስመሮም ለገሰ ዲሞክራሲያዊ የአስተዳደር ሥርዓት ያለውን የገዳ ሥርዓት ከመሠረቱ በመመርመር፣ የኦሮሞ ሕዝብ ሊያገኝ የሚገባውን ክብር እንዲያገኝ የደከሙና በአጠቃላይ ለሰብአዊ መብት መከበር የታገሉ ታላቅ ምሁር ነበሩ።
የገዳው ምሁር የፕሮፌሰር አስመሮም ለገሰን ከዚህ ዓለም በሞት መለየት ተከትሎ ምሁራንና የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች የተሰማቸውን ጥልቅ ሐዘን በመግለጽ ላይ እንደሚገኙ ከኦሮሚያ ባሕልና ቱሪዝም ቢሮ ያገኘነዉ መረጃ ያመላክታል፡፡