AMN የካቲት 30/2018
በአዲስ አበባ እና በሸገር ከተሞች ያለውን የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት አስተማማኝ ለማድረግ 4ኛው ምዕራፍ የዲስትሪቢዩሽን መስመር መልሶ ግንባታና ዐቅም ማሳደግ ፕሮጀክት እየተከናወነ ነው።
ሥራው እየተከናወነ የሚገኘው በ4 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር መሆኑን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የኮሙኒኬሽን ሥራ አስፈፃሚ አንዋር አብራር ገልጸዋል።
በዚህም መሠረት ሥራው 703 ኪሎ ሜትር የዲስትሪቢዩሽን ኔትዎርክ መልሶ ግንባታና ዐቅም ማሳደግን ያካተተ መሆኑን አመላክተዋል።
በተጨማሪም 2 ሺህ አዲስ የተለያየ ዐቅም ያላቸው ትራንስፎርመሮች ተከላና 2 ሺህ ነባር ትራንስፎርመሮችን ዐቅም የማሳደግ ሥራ የሚከናወንበት መሆኑን ጠቁመዋል።
በፕሮጀክቱ ከኃይል ማከፋፈያ ጣቢያ ወጪ የሚሆኑ 56 ማሰራጫ መስመሮችን መልሶ የመገንባትና የማሻሻል እንዲሁም ከተፈቀደው የኃይል አጠቃቀም በላይ ሲሆን መቆጣጠር የሚያስችሉ 62 የሎድ ብሬክ ስዊች ገጠማ ይከናወናል ብለዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት የፕሮጀክቱ አጠቃላይ የፊዚካል ሥራ አፈፃፀም 36 ነጥብ 74 በመቶ መድረሱን ጠቁመው፤ 2 ሺህ 857 የኮንክሪት ምሰሶዎች ተከላ ሥራም መከናወኑን አስታውቀዋል።
ሥራው ሲጠናቀቅ በአዲስ አበባና በሸገር ከተማ በዓመት በ100 ኪ.ሜ የመካከለኛ የኃይል ማሰራጫ መስመር ላይ የሚከሰተውን የኃይል መቆራረጥ ድግግሞሽ በ27 በመቶ ለመቀነስ ያስችላል ማለታቸዉን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
የትራንስፎርመር መቃጠልንም ወደ 2 በመቶ መቀነስ እንደሚያስችል አመላክተዋል።