
AMN – ታኅሣሥ 16/2017 ዓ.ም
በአዲስ አበባ ከተማ የማህፀን በር ካንሰር መከላከያ ክትባት ከታህሳስ 21 እስከ 25 በዘመቻ እንደሚሰጥ የአዲስ አበባ ከተማ ጤና ቢሮ አስታወቀ ።
የማህፀን በር ካንሰር መከላከያ ክትባት የሚሰጥበትን ሁኔታ አስመልክቶ የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ዮሃንስ ጫላ እና የከተማው ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዘላለም ሙላቱ(ዶ/ር) በጋራ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።
ክትባቱ ከታህሳስ 21 እስከ 25 2017 ዓ/ም ድረስ የሚቆይ ሲሆን እድሜያቸው ከ9 እስከ 14 ዓመት ለሆኑ ታዳጊ ሴት ልጆች በትምህርት ቤቶች እና በጤና ተቋማት የሚሰጥ ይሆናል ተብሏል።
የአዲስ አበባ ከተማ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዘላለም ሙላቱ (ዶ/ር) የማህፀን በር ካንሰር መከላከል ዘመቻው በመንግስትና በግል ትምህርት ቤቶች ለመስጠት ዝግጅት መጠናቀቁን ተናግረዋል ።
የተማሪ ወላጆች እና የሚመለከታቸው የማህበረሰብ ክፍሎች ጤናማ ትውልድ ለማፍራት በሚሰጠው የማህፀን በር ክትባት ካንሰር መከላከል ላይ ልጆችን በማስከተብ ሀላፊነታቸውን እንዲወጡ ጥሪ ቀርቧል።
በአዲስ አበባ ከተማ በዘንድሮው ዓመት 177 ሺ በላይ ለሚሆኑ ሴት ልጆች ክትባቱን ለመስጠት መታቀዱ ተመላክቷል።
በዘመቻው 1 ሺ 524 የጤና ባለሙያዎች የሚሳተፉበት ስለመሆኑም ዶ/ር ዮሃንስ ጫላ ተናግረዋል።
በመሀመድኑር አሊ