AMN ሚያዝያ 15/2018 ዓ.ም
የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ አረጋዊያን ዕድል ከተመቻቸላቸው መስራት ይችላሉ በሚል መሪ ቃል ለአረጋዊያን የገቢ ማስገኛ የሚውሉ ዶሮዎች፤ መኖ እና የዶሮ ኬጅ ድጋፍ አድርጓል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሴቶች ህጻናትና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ቆንጂት ደበላ አረጋዊያን የሀገር ባለውለታ የታሪክ ድልድይና ክብር ናቸው ብለዋል።
በሴፍቲኔት መርሃ ግብር በህብረተሰብ ተሳትፎ የቤት እድሳት ድጋፍና በምገባ መርሃ ግብር የከተማ አስተዳደሩ አረጋዊያንን ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ጠቅሰው ለአረጋዊያን የሚደረገው ድጋፍ አረጋዊያኑን ንቁና ውጤታማ ሆነው እንዲንቀሳቀሱ አንደሚያደርግ ተናግረዋል።
የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ታረቀኝ ወርቅነህ በበኩላቸዉ መንግስት አረጋዊያን ሆነው መንቀሳቀስ ለሚችሉ ሰርተው ገቢ የሚያገኙበትን ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ጠቅሰው ክፍለ ከተማውም ዶሮ ፤ መኖ እና ኬጅ መስጠቱን ተናግረዋል።

የአዲስ አበባ አረጋውያን ማህበር ፕሬዝዳንት አቶ ጌታቸው ክፍሉ መንግስት ለአረጋውያን እየሰጠ ያለው ትኩረትና ድጋፍ የሚያስመሰግን ነው ብለዋል።
ድጋፉ የተደረገላቸው አረጋዊያን በበኩላቸው አረጋዊያንን የሚያከብር ትውልድ ለራሱ ክብር የሚሰጥ እንደሆነ ተናግረዋል።
የተሰጣቸው የመስሪያ ድጋፍም አረጋዊያን መስራት እንደሚችሉ ማሳያ በመሆኑ በትጋት እንዲሰሩ እንደሚያበረታታቸው በመግለጽ በመንግስት ለተደረገላቸው ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል።

ምትኩ ተሾመ