ስሎቪኒያ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ መርሃ ግብሮችን ለመደገፍ የምታደርገውን ጥረት አጠናክራ እንደምትቀጥል የስሎቪኒያ ሪፐብሊክ ፕሬዚዳንት ናታሻ ፒርክ ሙሳር (ዶ/ር) ገለጹ።
የስሎቪኒያ ሪፐብሊክ ፕሬዚዳንት ናታሻ ፒርክ ሙሳር የቦስኮ ልጆች ማዕከልን ጎብኝተዋል።
ማዕከሉ በካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ስር ያለ ሲሆን ኑሯቸውን በጎዳና ያደረጉ ህፃናት የሙያና ስነምግባር ስልጠና እንዲያገኙ በማድረግ ራሳቸውን እንዲችሉና ከቤተሰባቸው ጋር እንዲቀላቀሉ እያደረገ የሚገኝ ነው።
ማዕከሉ ከዚህ ቀደም የተለያዩ የሙያ ስልጠናዎችን ሲሰጥ መቆየቱ ተገልጿል፡፡
ፕሬዚዳንቷ በጉብኝታቸው በስሎቪኒያ ህዝብና መንግስት ድጋፍ የሚተገበረውን ዘመናዊ የንብ ማነቢያ ሠርቶ ማሳያና የስልጠና መስጫ መርሃ ግብርን በይፋ አስጀምረዋል።
መርሃ ግብሩ በንብ ማነብ ላይ ያለውን ግንዛቤ ለማሳደግ የሚያግዝ በመሆኑ ስሎቪኒያ የምታደርገውን ድጋፍ አጠናክራ ትቀጥላለች ማለታቸዉን ኢዜአ ዘግቧል፡፡