የ90 ቀን እቅድ አካል የሆነ የክረምት በጎ ፍቃድ ስፓርታዊ ንቅናቄ ማስጀመሪያ መርሀ ግብር ተካሄደ።
ማህበረሰቡ በክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት በስፖርት የተሻለ እንዲሳተፉ ያስችል ዘንድ እንደ ከተማ የክረምት ስፓርታዊ ንቅናቄው በገላን ጉራ 2ኛ ደረጃ ት/ቤት ነው የተጀመረው።
ንቅናቄው የተጀመረው “ማስ ስፓርትን በትምህርት ቤቶች ባህል በማድረግ ጤናማ ንቁና ብቁ ትውልድ እንፈጥራለን” በሚል መሪ ቃል ነው።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዘላለም ሙላቱ (ዶ/ር)፤ ተማሪዎች በክረምት ወራት የእረፍት ጊዜያቸው 9 የስፓርት አይነቶች ተለይተው እንዲሰሩ በማድረግ ለቀጣይ የትምህርት ጊዜ ነቅተው እንዲጀምሩ ለማድረግ ይሰራል ብለዋል።
ተማሪዎች የክረምት ማጠናከሪያ ትምህርት እንዲወስዲና በጎ ተግባራትን እንዲያከናውኑ ከማድረግ ባሻገር የአረንጓዴ አሻራን እቅድ ለማሳካት ተማሪዎች እንዲሳተፉ ይደረጋል ነው ያሉት ዶ/ር ዘላለም።
የአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ትምህርት ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ከበደ ደሪባ በበኩላቸው፤ በአካልና በአዕምሮ የዳበረ ዜጋ ለመፍጠር ስፓርት ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
ንቅናቄውን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮና የአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ትምህርት ፅ/ቤት በጋራ በመሆን ነው ያዘጋጁት።
ከማስ ስፓርት በተጨማሪ ችግኝ የመትከል መርሀ ግብር ተካሂዷል።
የ90 ቀን እቅድ በርካታ ተግባራትን በማከናወን ጷግሜ 5/ 2017 ዓ.ም የሚጠናቀቅ ይሆናል።
በንጉሱ በቃሉ