AMN ጥር 19 ቀን 2018 ዓ.ም
የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ 1ሺህ 800 ሰዎችን በሕገ-ወጥ መንገድ በማዘዋወር የሁለት ሰዎች ህይወት እንዲያልፍ እና 15 ሰዎች የደረሱበት እንዳይታወቅ ያደረጉ እንዲሁም ከ2 ቢሊየን 160 ሚሊየን ብር በላይ ከተጎጂዎች በሕገ-ወጥ መንገድ የተቀበሉ 22 ተጠርጣሪዎችን በቁጥጥር ሥር ማዋሉን አስታወቀ፡፡
ከነዚህ መካከል ስድስት ተጠርጣሪዎች በሌሉበት ምርመራ ኣጣርቶ ለዐቃቤ ሕግ ልኳል፡፡
የፖሊስ የምርመራ መዝገብ እንደሚያስረዳዉ ተጠርጣሪዎቹ በሰዉ ልጅ ለመነገድ በማሰብ የወንጀል ቡድን በማደራጀት እና የቡድኑ አመራርና አባላት በመሆን በወንጀል ድርጊቱ ላይ መሳተፋቸዉን ፖሊስ በምርመራው አረጋግጧል፡፡
ተጠርጣሪዎቹ ወንጀሉን ለመፈፀም የወንጀል ቡድን አደራጅተው እና በሥራቸው ደላሎችን በመመልመል፤ በተለያዩ የሀገራችን አካባቢዎች በማሰማራትና የሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር የወንጀል መረብ በመዘርጋት ሰዎች በሊቢያ በኩል ወደ አዉሮፓ ገብተዉ የተሻለ ኑሮ እንደሚኖሩ በሐሰተኛ ተስፋ በማሳመን ሲልኩ መቆየታቸውን የፖሊስ ምርመራ መዝገብ ያስረዳል፡፡
ተጠርጣሪዎቹ ወደ ሱዳን ድንበር የሚያጓጉዙ ተቀጣሪዎችን በማዘጋጀት በሕገ-ወጥ መንገድ ተጎጂዎችን ከሀገር ሲያስወጡ መቆየታቸውን የገለፀው ፖሊስ ሰዎች ከኢትዮዽያ ድንበር ከወጡ በኋላ በዘረጉት የወንጀል መረብ አማካኝነት ወደ ሊቢያ ወስደዉ በመጋዘኖች ሲያጉሩ ቆይተዋል ብሏል፡፡
በሊቢያ የሚገኙ ተጠርጣሪዎች እና ግብረአበሮቻቸዉ በሚያስተዳድሯቸው መጋዘኖች ዉስጥ የሕገ-ወጥ ዝውውሩ ሰለባዎች በህይወት ለመቆየት ብቻ የሚያበቃ ምግብ እንዲያገኙ በማድረግ እና ወደ ቤተሰቦቻቸዉ ስልክ በማስደወል ከፍተኛ ገንዘብ በመጠየቅ ገንዘቡ እስኪከፈል ተጎጂዎችን መያዣ አድርገው እንደሚያቆዩ የፖሊስ ምርመራ መዝገብ አመላክቷል፡፡
በፍጥነት ገንዘብ መክፈል ላልቻሉ የተበዳይ ቤተሰቦች ተበዳዮችን እጅግ አሰቃቂ በሆነ ሁኔታ እየደበደቡ እና እያሰቃዩ ቪዲዮ በመቅረፅ ወደ ቤተሰቦቻቸዉ በመላክ ገንዘብ እንዲከፈል የስነልቦና ጫና ሲያደርጉ እንደ ነበረም የፖሊስ ምርመራ መዝገብ ያስረዳል፡፡
የተበዳይ ቤተሰቦች ገንዘብ አፈላልገዉ ለመክፈል ፍቃደኛ ሲሆኑ በቁጥጥር ሥር ከዋሉት የስምንቱን ተጠርጣሪዎች እና የሌሎች ግብረአበሮቻቸዉን የባንክ ሂሳብ በመጠቀም ገንዘብ ከተጎጂዎች በሕገ-ወጥ መንገድ ሲቀበሉ መቆየታቸውንም ፖሊስ ባደረገው ምርመራ እንደደረሰበት አስታውቋል።
በሕገ-ወጥ መንገድ ያገኙትን ከፍተኛ ገንዘብ ከሀገር እንዲሸሽ በማድረግ፤ በሀገር ዉስጥ እና በዉጪ ሀገር ቋሚና ተንቀሳቃሽ ሀብትና ንብረት እንዳፈሩ ፖሊስ በምርመራው ያረጋገጠ ሲሆን በተጠርጣሪዎቹ ስም ቤትና ተሽከርካሪ እንዲሁም ከ71 ሚሊየን ብር በላይ በባንክ አካውንታቸው መገኘቱን ፖሊስ ለኤኤምኤን በላከዉ መረጃ ገልጿል፡፡
የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ከፌደራል ፍትህ ሚኒስቴር፣ ከብሄራዊ መረጃ እና ደህንነት አገልግሎት፣ ከፋይናንስ ደህንነት አገልግሎት እና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት በመስራት በሕገ-ወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎች ላይ ጠንካራ ክትትል በማድረግ ተጠርጣሪዎችን ከተለያዩ የሀገራችን አካባቢዎች በቁጥጥር ሥር ማዋል መቻሉን የፖሊስ ምርመራ መዝገብ ያሳያል።