AMN ግንቦት 14/2018 ዓ.ም

ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸዉ ባሰፈሩት መልዕክት ዛሬ በከተማችን መሃል ፒያሳ ላይ ያስገነባነውን የገበያ ማዕከልና የትራንስፓርት ተርሚናል ለአገልግሎት ክፍት አድርገናል ብለዋል።
ፒያሳ በቀድሞ አጠራሩ “ዶሮ ማነቂያ” አካባቢን አፍርስን መልሰን አልምተን፥ አዘምነንና አስውበን ከ 101 በላይ የመሸጫ ሱቆች፥ ከመሬት በታች ሁለት ደረጃ ፓርኪንግ ፣ የታክሲ እና የአውቶቡስ ተርሚናል፥ ካፌ እና ሬስቶራንት፥ የመኪና የኤሌክትሪክ ቻርጅ አገልግሎት መስጫ፥ እንዲሁም ኘላዛና ፋውንቴን ጨምሮ 2 ዘመናዊ ሊፍት፥ ቢሮዎች፥ ክሊኒክ እና ፋርማሲ፣ ዘመናዊ የእሳት አደጋ መከላከያ መሳሪያዎች፥ የደህንነት መቆጣጠርያ ተገጥመውለት ሱቆቹና ካፍቴሪያዎቹ ለአካባቢው ለተነሽዎች በእጣ አስተላልፈናል ብለዋል።

የአድዋ የገበያ ማዕከልና የትራንስፓርት ተርሚናል በመጨናነቅ፣ ግፊያ፣ እንግልት፣ በፀሀይ፥ በዝናብ እና አቧራ ላይ ሲንገላታ ለነበረዉ ህዝባችን ንፁህ ምቹ እና ስርዓት ያለው የትራንስፖርት አገልግሎት መስጫም አድርገነዋል ።
ፒያሳ ኣካባቢ የኮሪደC ልማት የጀመርንበት ነው። ዛሬ ፒያሳ የጋራ ታሪካችንን “የአድዋ ድል መታሰቢያን” የገነባንበት እና የአገራት መሪዎች ለጀግኖች ሰማእቶቻችን የአበባ ጉንጉን የሚያኖሩበትን ጨምሮ በርካታ የጋራ መገልገያ እና የቱሪስት ስበትን የጨመሩ መሰረተ ልማቶች የሰራንበት ታሪካዊ ቦታ ሆኗል ሲሉ ገልጸዋል።

ይህ የዛሬውን ፕሮጀክት በተቀመጠለት ጊዜና የጥራት ደረጃ ተጠናቆ ለአገልግሎት እንዲበቃ ላደረጋችሁ በሙሉ ላቅ ያለ ምስጋናዬን አቀርባለሁ ሲሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ መልዕክት አስተላልፈዋል።