የሚያዝያ እና ግንቦት የጠቅላይ ሚኒስትሩ ቁልፍ ተግባራት ቅኝት ከምስል ጋር!

You are currently viewing የሚያዝያ እና ግንቦት የጠቅላይ ሚኒስትሩ ቁልፍ ተግባራት ቅኝት ከምስል ጋር!

AMN – ግንቦት 26/2018 ዓ.ም

የኢንዱስትሪ መስፋፋት እና ኢኮኖሚያዊ ሉዓላዊነት

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ነጻነት ለማረጋገጥ፣ የረጅም ጊዜ የኢንዱስትሪ ዕድገትን እና ገቢ ምርቶችን በሀገር ውስጥ መተካትን መሠረት ያደረጉ የተለያዩ የአምራች ዘርፍ እንቅስቃሴዎችን በንቃት መርተዋል።

በዚህም የፋይናንስ አቅርቦትን ማሳደግ ላይ ያተኮረውን 4ኛውን የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ በይፋ የከፈቱ ሲሆን፣ የወጣቶችን የሥራ ዕድል ለማስፋፋትም በአዲስ አበባ የሚገኘውን የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ መርቀው ከፍተዋል።

በተጨማሪም የታዳሽ ኃይል አቅምን ለማሳደግ አዲስ ሥራ የጀመረውን የጎበዜ የሶላር ሴል ማምረቻ ፋብሪካን እንዲሁም፣ የአካባቢውን ጥሬ ዕቃዎች በመጠቀም የገቢ ምርቶችን ለመተካት ያለመውን በሞጆ ከተማ የሚገኘውን የግራንደር የሴራሚክ ማምረቻ ፋብሪካንም መርቀው ከፍተዋል።

የላቀ የጤና ሥርዓትና ዘመናዊ አገልግሎቶች

ኢትዮጵያ በልዩና በላቀ የሕክምና ብቃት ቀጠናዊ ማዕከል ለመሆን የምታደርገውን ስትራቴጂካዊ ጉዞ ግብ ለማሳካት ጠቅላይ ሚኒስትሩ እጅግ በዘመናዊ የሕክምና ቴክኖሎጂዎች እና በሮቦቲክስ የታገዘውን፣ እንዲሁም የካንሰር እና የልብ ሕመሞችን በሀገር ውስጥ ለማከም የተገነባውን ዘመናዊውን የላፍቶ ሆስፒታል በአዲስ አበባ በይፋ መርቀው ከፍተዋል።

በተጨማሪም በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ውስጥ በሕክምና ሥልጠና ላይ ለሚገኙ የሩዋንዳ እና ከሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ለመጡ የሕክምና ባለሙያዎች ይፋዊ የእራት ግብዣ አድርገዋል።

መሠረተ ልማት፣ ዘላቂ አገልግሎቶች እና ትራንስፖርት

ጠቅላይ ሚኒስትሩ የንግድና ማኅበራዊ ትስስርን የሚያጠናክረውንና የኢትዮጵያ አየር መንገድ 24ኛ የአገር ውስጥ መዳረሻ የሆነውን አዲሱን የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያን መርቀዋል።

በተጨማሪም በጎመሌ ወረዳ የሚገኘውን የደሴ ጎራ ግድብን ጨምሮ የፊና ኦሮሚያ መስኖ ፕሮጀክቶች መጠናቀቃቸውን የተከታተሉ ሲሆን፣ ንጹሕ ውኃ ለማቅረብና ለረጅም ጊዜ የሚዘልቅ የድርቅ መቋቋም አቅምን ለመገንባት የተነደፈውን መጠነ-ሰፊ የቦረና የውኃ አቅርቦት ፕሮጀክት ማስፋፊያ ሥራ ጉብኝትንም በበላይነት መርተዋል።

የግብርና ትራንስፎርሜሽን እና የምግብ ሉዓላዊነት

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እና የክላስተር እርሻን ለማስፋፋት በዋና ዋና የግብርና ክልሎች የመስክ ጉብኝት ያደረጉ ሲሆን፣ በዚህም የሀገር ውስጥ የዩሪያ ማዳበሪያ ምርትን ለማሳደግ የታቀደውን የፋብሪካ ግንባታ ሂደት ለመገምገም ከአሊኮ ዳንጎቴ ጋር ወደ ጎዴ ተጉዘዋል።

በተጨማሪም በምሥራቅ ቦረና ዞን በሺዎች የሚቆጠሩ አባወራዎችና እማወራዎችን ያሳተፈውን መጠነ ሰፊ የክላስተር ግብርና ንቅናቄ የጎበኙ ሲሆን፣ በሰሜን ሸዋ ዞን በብዙ ሄክታር መሬት ላይ የሚገኘውን የስንዴ እርሻ ልማትም ጎብኝተዋል።

የሚዲያ እና የብሔራዊ ፖሊሲ ሉዓላዊነት

የመንግሥት ተቋማትን እና የብሔራዊ ፖሊሲ ነጻነትን ለማጠናከር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ሀገራዊ የምክክር መድረኮች ላይ ተገኝተዋል።

ዲጂታላይዝድ ወደሆነ እና ራሱን ወደቻለ የስታቲስቲክስ ማዕቀፍ የሚደረገውን ሀገራዊ ሽግግር ለመደገፍ “የመረጃ ሉዓላዊነት ለፖሊሲ ነጻነት” በሚል መሪ ቃል በተዘጋጀው ብሔራዊ ጉባኤ ላይ የተገኙ ሲሆን፤ በተጨማሪም የብሔራዊ ምክክር ኮሚሽን ወደ ትግበራ ምዕራፍ ሊሸጋገር የቀረበውን ይፋዊ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ተቀብለዋል።

በዚሁ ወር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለብሔራዊ ልማት የሚረዱ የሚዲያ ሥነ-ምግባር ሙያዊ መመሪያዎችን አስምረው የተናገሩበት እና “የሚዲያ እምርታ ለሀገር ግንባታ” በተሰኘው ብሔራዊ መድረክ ላይ ለሚዲያ ዘርፍ መሪዎችና ባለሙያዎች ንግግር አድርገዋል።

የባህል ጥበቃ እና አካባቢያዊ እንክብካቤ

በኦሮሚያ ክልል የገዳ ሥርዓት ታሪክንና ፍልስፍናን ለመጠበቅ በያቤሎ ከተማ የተገነባውን የቦረና ባህል ማዕከል ጠቅላይ ሚኒስትሩ መርቀው የከፈቱ ሲሆን፣ ማዕከሉ በ”መደመር” መጽሐፍ ሽያጭ ገቢ የተደገፈ እንደሆነም ይታወሳል።

ከዚህ ጎን ለጎን፣ የዱር እንስሳትና ብዝሃ-ሕይወት መጠበቂያ ሆኖ የሚያገለግለውን የቦረና ብሔራዊ ፓርክን መርቀው ከፍተዋል።

ዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲ እና የሁለትዮሽ ግንኙነቶችን የሚያጠናክሩ ማዕቀፎች

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ የኢትዮጵያን ዲፕሎማሲያዊ አጋርነት ለማጠናከር በብሔራዊ ቤተ መንግሥት ከፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ጋር የተወያዩ ሲሆን፣ በብድር እና በተለያዩ ዘርፎች አጋርነት ላይ ስምምነቶችን አድርገዋል።

በተጨማሪም በናይሮቢው አፍሪካ ፎርዋርድ ጉባኤ ላይ የተሳተፉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ኢትዮጵያ ከተገበረቻቸው የልማት ሞዴሎች ልምድ ከማካፈላቸውም ባለፈ ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF) ዋና ሥራ አስፈጻሚ ክሪስታሊና ጆርጂየቫ ጋር የኢኮኖሚ ምክክር አድርገዋል።

በዚሁ ወር በጅቡቲ የፕሬዚዳንት እስማኤል ዑመር ጌሌን በዓለ-ሲመት የታደሙ ሲሆን፣ ከኔዘርላንድስ ጠቅላይ ሚኒስትር ሮብ ዬተን ጋር የስልክ ውይይት አድርገዋል።

በመጨረሻም የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት 80ኛ ዓመት መታሰቢያን ምክንያት በማድረግ የቴምብር ስብስብ ይፋ አድርገዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት

#PMOEthiopia

See less

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review