የአዲስ አበባ የተቀናጁ የልማት ስራዎች የከተማዋን ተወዳዳሪነት እያሳደጉ ናቸው

You are currently viewing የአዲስ አበባ የተቀናጁ የልማት ስራዎች የከተማዋን ተወዳዳሪነት እያሳደጉ ናቸው

AMN ግንቦት 4/2018

በአዲስ አበባ እየተከናወኑ የሚገኙት የተቀናጁ የከተማ ልማት ስራዎች የከተማዋን ዓለምአቀፍ ተወዳዳሪነት ከመጨመር ባለፈ የነዋሪዎችን የኑሮ የሚያሻሽሉ መሆናቸውን የከተማ ንድፍ እና የኪነ-ህንጻ ምሁራን ገለጹ።

ኤን ቢ ሲ ኢትዮጵያ (NBC Ethiopia) “አዲሲቱ አዲስ” በሚል ርዕስ ያዘጋጀው የውይይት መድረክ በመካሄድ ላይ ይገኛል።

“የአዲስ አበባ ዘመናዊ ጉዞ ታሪካዊ ዳራ እና ልምዶች” በሚል ርዕስ የመወያያ ጽሁፍ ያቀረቡት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኪነ-ህንጻ መምህር ዳዊት በንቲ፤ አዲስ አበባ በምስረታዋ ወቅት በታቀደ የከተማ ፕላን ያልተጀመረች መሆኗን አስታውሰዋል። በተለያዩ ዘመናት ከተማዋን ለማዘመን ሙከራዎች ቢደረጉም፣ በሚፈለገው ደረጃ መሰረታዊ ለውጥ ማምጣት እንዳልተቻለ ጠቁመዋል።

ይሁን እንጂ ከ2010 ዓ.ም ወዲህ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች የከተማዋን ገጽታ በከፍተኛ ደረጃ እየቀየሩ መሆኑን ጠቅሰው፤ በተለይም ሰፋፊና ዘርፈ-ብዙ አገልግሎት የሚሰጡ ፓርኮችና አረንጓዴ ስፍራዎች መገንባታቸው የነዋሪዎችን የአኗኗር ዘይቤ እየቀየሩ መሆኑን አብራርተዋል።

በተጨማሪም የከተማዋ መገለጫ የሆኑት የወንዝ ዳርቻ ልማቶች፣ የብስክሌት እና የእግረኛ መንገዶች ለነዋሪዎች ምቹ ከባቢ መፍጠራቸውን አብራርተዋል።

በሌላ በኩል “የከተማ ትራንስፎርሜሽን እሳቤዎች፣ ትግበራ እና አንድምታዎች በአዲስ አበባ” በሚል ርዕስ ጽሁፍ ያቀረቡት የከተማ እና ቀጣናዊ ፕላኒንግ ከፍተኛ ተመራማሪ ኢንጂነር እሸትአየሁ ክንፉ፤ የአዲስ አበባ እድገት በታሪካዊ የፖለቲካ ለውጦች ላይ የተንተራሰ መሆኑን ገልጸዋል።

በቀደሙት ዓመታት የከተማዋ አሰፋፈር ለቴክኖሎጂ እና ለዘመናዊ አገልግሎት አመቺ እንዳልነበረ አስታውሰው፤ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ግን የከተማ ማደስ ስራው ፍትሃዊ፣ ተወዳዳሪ እና ለኑሮ ምቹ ከተማን ለመፍጠር ያለመ መሆኑን ገልጸዋል።

እነዚህ ስራዎች አዲስ አበባን በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላትን ተቀባይነት ከፍ እያደረጉት እንደሚገኙም አመልክተዋል።

የኤንቢሲ (NBC) ምክትል ዋና ስራ አስኪያጅ ዘካርያስ ብርሀኑ በመክፈቻ ንግግራቸው፣ አዲስ አበባ አሁን ላይ ግዙፍና ተጨባጭ ለውጥ እያስመዘገበች መሆኗን ገልጸዋል።

በመሆኑም በመድረኩ የከተማዋ የልማት እንቅስቃሴዎች ከዓለምአቀፍ ተሞክሮዎች ጋር በማነጻጸር እንደሚዳሰሱና በተለያዩ የጥናት ጽሁፎች ላይ ውይይት እንደሚደረግ ማስታወቃቸዉን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review