ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ የምትጫወተው ግንባር ቀደም ሚና የሚደነቅ ነው- አፈ-ጉባኤ ሳሂባ ጋፋሮቫ (ፕ/ር)

AMN- ሐምሌ 23/2018 ዓ.ም

ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ እና በአህጉሩ የምትጫወተው ግንባር ቀደም ሚና፣ የአንድነትና የትብብር ማዕከልነቷን በግልጽ እንድገነዘብ ረድተውኛል ሲሉ የአዘርባጃን ሪፐብሊክ ብሔራዊ ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ (ፕ/ር) ሳሂባ ጋፋሮቫ ገለጹ።

አፈ-ጉባኤ ሳሂባ ጋፋሮቫ (ፕ/ር) በውጭ ጉዳይ ኢንስትቲዩት በተዘጋጀ በፓርላመንታሪ የዲፕሎሚሲ እና የባለብዙ ወገን ውይይት ላይ እንደተናገሩት፣ የአዘርባጃንና የኢትዮጵያ ግንኙነት በፈጣን ሁኔታ እየተጠናከረ መጥቷል።

አፈ-ጉባኤዋ በቆይታቸው ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)፣ ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ ታገሰ ጫፎ እና ከፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር ጋር ፍሬያማ ውይይቶችን ማድረጋቸውን ጠቁመዋል።

‌‎እነዚህ ውይይቶች ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ እና በአህጉሩ የምትጫወተውን ግንባር ቀደም ሚና፣ የአንድነትና የትብብር ማዕከልነቷን በግልጽ እንድገነዘብ ረድተውኛል ብለዋል።

‌‎በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው የከፍተኛ አመራሮች ግንኙነት እየጎለበተ መምጣቱንም አስረድተዋል።

‎ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአዘርባጃን ይፋዊ ጉብኝት በማድረግ ከፕሬዚዳንት ኢልሃም አሊዬቭ ጋር የሁለትዮሽ ግንኙነቶችን የሚያጠናክሩ ስምምነቶችን መፈራረማቸውን አስታውሰዋል።

‎በተጨማሪም ‎የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ በአዘርባጃን ጉብኝት ማድረጋቸው የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት እያደገ ስመለምጣቱ ማሳያ ነው ብለዋል።

‎የሄይዳር አሊዬቭ ፋውንዴሽን ምክትል ፕሬዚዳንት ሌይላ አሊዬቫ በኢትዮጵያ ያደረጉት ጉብኝት የባህል እና ሰብዓዊ ትስስሩን ማጠናከሩን አሳታውሰዋል።

‎በኢትዮጵያ ፍላጎት እና አቅም ላይ ተመስርቶ የበለጸገውን መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ተዘዋውረው መጎብኘታቸውንም ጨምረው ጠቅሰዋል።

‎መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ኢትዮጵያ የራሷ ስኬት እና የአገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመን ያደረገችው ቁርጠኝነት ማሳያ ነው ብለዋል።

‎ኢትዮጵያ በፈጣን የምጣኔ ሀብት እድገት ላይ የምትገኝና በአህጉራዊ እና አለምአቀፋዊ መድረክ የምትጫወተው ሚና የሚደነቅ መሆኑን ማስታወቃቸውንም ኢዜአ ዘግቧል።

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review