የኢትዮጵያ ማንሰራራት የአፍሪካን ሕዳሴ ያበሰራል!- የኢፌዴሪ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት

You are currently viewing የኢትዮጵያ ማንሰራራት የአፍሪካን ሕዳሴ ያበሰራል!- የኢፌዴሪ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት

AMN – መስከረም 5/2019 ዓ.ም

ኢትዮጵያ አዲሱን ዓመት ብሔራዊ ጥቅሞቿን በማስቀደምና የአፍሪካውያን እውነተኛ ድምፅ በመሆን ጀምራዋለች።

በዓለም አቀፍ ተለዋዋጭ የጂኦፖለቲካ ውጥረት ውስጥ ጽኑና ገለልተኛ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲን በመከተል የብሪክስ አባል መሆን የቻለችው ኢትዮጵያ፣ በሕንድ ኒው ዴልሂ በተካሄደው 18ኛው የብሪክስ መሪዎች ጉባኤ ላይ አህጉራዊ አርአያነቷንና ስትራቴጂካዊ ተሰሚነቷን በተግባር አስመስክራለች።

“ጽናትን፣ ፈጠራን፣ ትብብርን እና ዘላቂነትን መገንባት” በሚል መሪ ቃል የተካሄደው ይህ ጉባኤ፣ ኢትዮጵያ ከአባልና አጋር ሀገራት ጋር ያላትን ሁለገብ ትስስር ወደ ላቀ ከፍታ ያሸጋገረና ፍትሃዊና አካታች ዓለም አቀፍ ሥርዓት እንዲገነባ ያላትን ቁርጠኝነት በግልጽ ያሳየ ምዕራፍ ሆኗል።

ኢትዮጵያ በጉባኤው መድረክ ላይ ባነጸባረቀችው አቋም፣ ሀገራት ቀውሶች ከመከሰታቸው በፊት የመቋቋም አቅም ሊገነቡ እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥታለች።

በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ባደረገችው ጥረት ከውጭ ለእርዳታ ከሚገባ የስንዴ ጥገኝነት ሙሉ በሙሉ መላቀቋን ይፋ ያደረገች ሲሆን የብሪክስ የሰብል ልውውጥ ማዕቀፍ (BRICS Grain Exchange) እንደ አምራችም ሆነ አቅራቢ ሆና ለመሳተፍ ዝግጁ መሆኗን አረጋግጣለች።

በመድረኩ ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂና ፈጠራ ዘርፍ የዲጂታል መሠረተ ልማት፣ ዲጂታል መታወቂያ፣ የክፍያ ሥርዓቶች እና አስተማማኝ የመረጃ ልውውጥ አውታሮችን በስፋት እየገነባች መሆኗን አስገንዝባለች።

ለአፍሪካ የነገውን የቴክኖሎጂ ዘመን በባለቤትነት ለመምራት የሚያስችለውን «የመደመር ሰው ሠራሽ አስተውሎት ዩኒቨርሲቲ» እያቋቋመች መሆኗን በመግለጽ፣ ከብሪክስ ተቋማት ጋር በጋራ ለመሥራት ያላትን ዝግጁነት አረጋግጣለች።

አፍሪካ የበርካታ ማዕድናት ሀብት ባለቤት መሆኗን በማስታወስም፣ የማዕድን ሀብት ለኢነርጂ ሽግግር፣ ለላቀ ማኑፋክቸሪንግ እና ለዲጂታል ኢኮኖሚ ወሳኝ መሆኑን ኢትዮጵያ አንጸባርቃለች።

የብሪክስ አባል ሀገራት የካፒታል፣ የቴክኖሎጂ እና የገበያ አማራጭ በመያዛቸው እነዚህን ሀብቶች አቀናጅቶ ለመጠቀምና በጥሬ ሀብቱ ላይ እሴት ለመጨመር ትልቅ እድል እንደሚፈጥር አመልክታለች።

ኢትዮጵያ በጤናው ዘርፍ የማምረት አቅሟን እያስፋፋች መሆኗን፣ እንዲሁም በማዕድናት፣ በታዳሽ ኢነርጂ እና እያደገ ባለው የኢንዱስትሪ አቅም ላይ አጋርነቶችን ለመፍጠር ዝግጁ መሆኗን አረጋግጣለች።

በተጨማሪም የኢትዮጵያ አየር መንገድ አፍሪካን ከዓለም ጋር የሚያገናኝ ትልቅ ዕድል መሆኑን፣ ለጎረቤት ሀገራት የሚደረገው የኃይል አቅርቦት እና አዲስ አበባ የአፍሪካ ህብረት መቀመጫ መሆኗ ለአህጉራዊና ዓለም አቀፍ ትስስር ያላትን አበርክቶ በግልጽ በማስመዝገብ መድረኩን ተጠቃማበታለች።

ከዓለም አቀፍ የፋይናንስ ስርዓት ጋር በተያያዘ ኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሪፎርም እያከናወነችና የውጭ ዕዳዋን ለማሸጋሸግ እየሰራች መሆኗን ገልጻ፤ በፈተና ውስጥ ለሚገኙ ኢኮኖሚዎች የዕዳ አከፋፈል ሂደት ፈጣን፣ ግልጽ እና ተገማች መሆን እንዳለበት አሳስባለች።

እንዲሁም በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ውስጥ ያላቸው ውክልና ፍትሃዊ፣ ተደማጭነታቸውን ያረጋገጠ እና ተጨባጭ ውጤት የሚያመጣ መሆን እንዳለበት ጠንካራ ጥሪ አቅርባለች።

በጉባኤው ባደረገችው ንቁ ተሳትፎም ሀገራችን የዓለም ንግድ ድርጅት አባል እንድትሆን፣ በዓለም አቀፍ የሲቪል አቪዬሽን ድርጅት (ICAO) ምክር ቤት ተጨማሪ መቀመጫ እንድታገኝ፣ እንዲሁም የዓለም አቀፉ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤን (COP32) በአዲስ አበባ እንድታዘጋጅ ድጋፍ አግኝታለች፤ የኒው ዴቨሎፕመንት ባንክ (NDB) ቢሮ በአዲስ አበባ እንዲከፈት እና ቅድሚያ የሚሰጣቸውን ጉዳዮች ወደ ስምምነት የሚቀይር «የብሪክስ አስተባባሪ» እንዲቋቋም ያቀረበቻቸው ምክረ ሀሳቦች ሰፊ ተቀባይነት አግኝተዋል።

ከብሪክስ መድረክ ጎን ለጎን ከተከናወኑ ሰፊ የዲፕሎማሲ ሥራዎች መካከል ከዓለም መሪዎች ጋር የተደረጉት ውይይቶች ሀገራዊ ጥቅሞችን ከማስጠበቅና አጋርነትን ከማጠናከር አንፃር ትልቅ ስኬት የተመዘገበባቸው ነበሩ።

ከሩሲያ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ጋር በኢትዮጵያና ሩሲያ መካከል ያለውን ስትራቴጂካዊ አጋርነት ይበልጥ ማጠናከር በሚቻልባቸው ጉዳዮች ዙሪያ ፍሬያማ ውይይት ተደርጓል።

ውይይቱ በመከላከያና ደኅንነት፣ በንግድና ኢንቨስትመንት፣ በትምህርት፣ ቴክኖሎጂ እንዲሁም በባህልና ሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት መስኮች ያለውን ትብብር ለማሳደግ የጋራ ቁርጠኝነት የተረጋገጠበት ነበር።

በተጨማሪም ለኮፕ 32 በሚደረገው ዝግጅት፣ በአየር ንብረት ለውጥ እና በልማት ግቦች ዙሪያ ትብብራችንን ለማጠናከር የሚያስችል ስምምነት መፍጠር ተችሏል።

ከሕንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ጋርም በመከላከያ ትብብር ማሳደግ፣ በቴክኖሎጂ ሽግግር፣ በአቅም ግንባታ እና በማዕድን ልማት ዙሪያ ውይይት የተደረገ ሲሆን፤ የዘመናት ታሪካዊ ትስስራችንን ወደተግባራዊ የኢኮኖሚና ልማት ምዕራፍ ማሸጋገር ተችሏል።

በተጨማሪም ከማሌዢያ ጠቅላይ ሚኒስትር አንዋር ኢብራሂም ጋር በኢንቨስትመንት፣ ቱሪዝም፣ የታዳሽ ኃይል አጋርነትና በአምራች ዘርፍ ተሞክሮዎች ዙሪያ ውይይት ተደርጎ ለሀገር ውስጥ ልማት የሚሆን ትልቅ በር ተከፍቷል።

ከአቡ ዳቢ አልጋ ወራሽ ልዑል ሼህ ኻሊድ ቢን ሙሀመድ ቢን ዛይድ አል ናህያን ጋር በብሪክስ ቅድመ-አጀንዳዎችና በሁለገብ ትብብር ላይ ውይይት የተደረገ ሲሆን፤ ከኢራኑ ፕሬዚዳንት መስዑድ ፔዜሽኪያን ጋርም በቀይ ባሕር አካባቢ ወቅታዊ ሁነቶች እና በቀጣናው የደኅንነት መረጋጋት እንዲሁም በወል ተጠቃሚነት ላይ የተመሠረተ የንግድ፣ የኢኮኖሚና ልማት ልውውጦቻችንን ይበልጥ ለማስፋፋት በጋራ ለመሥራት ስምምነት ላይ ተደርሷል።

በአጠቃላይ፣ ኢትዮጵያ በ18ኛው የብሪክስ የመሪዎች ጉባኤ ላይ ያከናወነቻቸው ስትራቴጂካዊ የዲፕሎማሲ ሥራዎችና ያስመዘገበቻቸው ተጨባጭ ውጤቶች የሀገሪቱን የረጅም ጊዜ የዲፕሎማሲና የኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን እውን የሚያደርጉ ወሳኝ ምሶሶዎች ናቸው።

መንግሥት በዚህ ታሪካዊ መድረክ ኢትዮጵያ የብሪክስ አባልነቷን በመጠቀም ስትራቴጂካዊ ጥቅሟን በድፍረት የምትጠይቅ፤ ለአፍሪካ ልማት፣ ሰላም እና ፍትሃዊ ዓለም አቀፍ ትብብር የቆመች አስተማማኝ አጋር መሆኗን በተግባር አስመስክሯል።

የኢትዮጵያ ማንሰራራት የአፍሪካን ሕዳሴ ያበሰራል!

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review