3ኛው የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 4ኛ መደበኛ ጉባኤ የሁለተኛ ቀን ውሎ ቀጥሏል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ ፍርድ ቤቶች 2017 ዕቅድ አፈፃፀም ለምክር ቤቱ ያቀረቡት የአዲስ አበባ ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤቶች ፕሬዝዳንት አቶ ተስፋዬ መለሰ ቀልጣፋ ፣ውጤታማና ተደራሽት ያለው አገልግሎትን መስጠት የፍርድ ቤቶች ተቀዳሚ ተግባር መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በበጀት ዓመቱ መዛግብት የማጥራት ዕቅድ 97 በመቶ ለመፈጸም ታቅዶ 98 በመቶ መከናወኑንም አስታውቀዋል፡፡
የቅልጥፍና መለኪያ በተቀመጠው ጊዜ መሠረት ለጉዳች ውሳኔ መስጠት ነው፤ በዚህ መሠረትም በስታንዳርድ መሠረት 89 በመቶ የፍትሀብሔር ጉዳዮች ውሳኔ አግኝተዋል ብለዋል፡፡
በ2017 በጀት ዓመት ውሳኔ ሳያገኙ ወደ ቀጣይ በጀት ዓመት የተላለፉት በይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት እና በመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 3ሺ 32 ጉዳዮች መኖራቸውንም ገልጸዋል፡፡
18 ዓለም አቀፍ የአገልግሎት እርካታ ደረጃ ምዘና መስፈርት መሠረት ከ85 በመቶ በላይ አፈፃፀፀም ማስመዝገብ ከፍተኛ መሆኑን ያስገነዘቡት ፕሬዝዳንቱ በበጀት ዓመቱ የተሻ ውጤት የተገኘባቸውን ክንውኖችም በሪፖርታቸው አመላክተዋል፡፡

ባለጉዳይን ያለ ምንን ልዩነት በትህት እና አክብሮት ማገልገል፣ የዳኞች እና ሰራተኞች ያለ ጉቦ ማገልገል፣ የፍርድ ቤቶች ኃላፊዎች ሙስናና ብልሹ አሠራርን ለመካላከል ያላቸው ተነሳሽነት ፣ የሥነ ምግብር ጉድለት ያሳዩትን ተጠያቂ ለማድረግ ያለው ቄርጠኝነት እና በመሳሰሉት መስፈርቶች ከፍተኛ ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል፡፡
በአንፃሩ ግልፅ ችሎት አለመኖር፣ የቀረቡ ክርክሮችና ማስረጃዎችን በአግባቡ አለመመዘን፣ በቴክኖሎጂ የታገዘ አገልግሎት ውስንነት፣ ተደጋጋሚ ቀጠሮ መስጠት፣የቋንቋ አስተርጓሚ አለመኖር፣ ነፃ የህግ አገልግሎት አለመኖር እንዲሁም ጉዳዮች በእርቅ እንዲያልቁ በፍርድ ቤት ተገቢው እድል አለመስጠት በሚሉት መመዘኛዎች ደግሞ ፍርድ ቤቱ ከዓለም አቀፍ ምዘና በታች መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
የከተማ ፍርድ ቤቶች የሪፎርም ሥራዎች በትግበራ ላይ እንደሚገኙ ያነሱት ፕሬዝዳንቱ በዓመቱ በጥንካሬ የተመዘገቡ ጠንካራ ጎኖችን በማስቀጠል እና በክፍተት የተለዩትን ደግሞ በበማረም ለተሻለ ውጤት እንደሚሰራ ገልፀዋል፡፡
የፍርድ ቤቶችን ሥራ በተለይም በቴክኖሎጂ ማስደገፍ ላይ የታየውን ውስንነት ለማሻሻል በሪፎርሙ በስፋት እየተሰራበት ይገኛልም ብለዋል፡፡
የበጀት አመቱን የፍርድ ቤቶች የአፈፃፀም ሪፖርት ያዳመጠው ምክር ቤቱ በቀረበዉ ሪፖርት ላይ የተሰጡትን የአባላቱን ሀሳብ እና አስተያየት ካዳመጠ በኋላ ሪፖርቱን በሙሉ ድምፅ አፅድቋል፡፡