ግራንድ የአፍሪካ የተቋማት እና የአመራር ሽልማት ድርጅት፣ በኢትዮጵያ ውስጥ በተለያዩ የልማት መስኮች የላቀ አፈፃፀም ላሳዩ ተቋማትና አመራሮች እውቅና የሚሰጥበት 20ኛው የሽልማት መርሃ-ግብር ታኅሣሥ 12 ቀን 2018 ዓ.ም የፊታችን እሁድ እንደሚካሄድ አስታወቀ።
የሽልማት ድርጅቱ በዋናነት በኢትዮጵያ ውስጥ በአምራችነት እና በአገልግሎት ዘርፍ የተሰማሩ፣ ለሀገርና ለወገን የሚጠቅሙ ስራዎችን የሰሩ ተቋማትንና መሪዎችን የሚያበረታታ ነው።
የድርጅቱ ፕሬዝዳንት እና ዋና ስራ አስፈፃሚ ግርማ በቀለ ለኤ ኤም ኤን ዲጂታል እንደገለጹት፣ ተሸላሚዎቹ የሚመረጡት ተቋሙ ባወጣው ጥብቅ መስፈርት መሠረት ነው ብለዋል።

ተቋማትና አመራሮች በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪና ተቀባይነት እንዲኖራቸው ማድረግ፣ጥራት ያለው ምርትና አገልግሎት እንዲቀርብ ማበረታታት አላማ ያደረገ የእውቅና መርሀ ግብር መሆኑን ዋና ስራ አስፈፃሚው ተናግረዋል።
ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ምርቶች የመተካት (Import Substitution) ጥረትን ማገዝ አላማ ያደረገ መሆኑም ተገልጿል።
በመርሃ ግብሩ ላይ የድርጅቱ የበላይ ጠባቂ የቀድሞው የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ (ዶ/ር) እንደሚገኙ የገለፁት የድርጅቱ የሽልማት ዘርፎች እና ምዘና ስራ አስኪያጅ መለሰ መካሻ (ዶ/ር) ከፍተኛ የመንግስት ስራ ሃላፊዎች ፣ ታዋቂ ግለሰቦች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እንደሚታደሙም ገልፀዋል።
የሽልማት መርሃ-ግብሩ በነገው ዕለት ታኅሣሥ 12 /2018 ዓ.ም የሚካሄድ ሲሆን፣ በአዲስ ሚዲያ ኔትወርክ (AMN) በቀጥታ ስርጭት ለተመልካች ይደርሳል፡፡
በሔለን ተስፋዬ