AMN ግንቦት 6/2018
በሕይወት መስዋዕትነት የተገኘ ሉዓላዊነትን በላባችን ምሉዕ ማድረግ ይገባናል ሲሉ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተስፋሁን ጎበዛይ ገለፁ።
“ከተረጅነት ወደ ምርታማነት” በሚል መሪ ሃሳብ በሐዋሳ ከተማ የውይይት መድረክ ተካሂዷል።
በመድረኩም የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ እውነቴ አለነ፣ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) ፣ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተስፋሁን ጎበዛይ እና የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) ተገኝተዋል።

እንዲሁም በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ ኡስማን ሱሩር ፤ የሲዳማ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ መምሩ ሞኬ፤ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሸን ኮሚሽነር ወገኔ ብዙነህ፤ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር ለማ መሰለ(ዶ/ር) እና ሌሎች የሥራ ኃላፊዎችና የግብርና ሙያተኞች ተገኝተዋል።
በዚሁ ወቅት አቶ ተስፋሁን ጎበዛይ እንዳሉት ከተረጂነት ወደ ምርታማነት መሻገር የሀገር ወሳኝ አጀንዳ ስለመሆኑ ገልፀዋል።
ኢትዮጵያ የመሬት፣ አየር ፀባይ፣ውሃ ፤ የሰው ሀብት እንዲሁም የነፃነትና የሉዓላዊነት ታሪክ ያላት ሀገር ብትሆንም ላለፉት ሰባት አስርት ዓመታት ስንዴ ሲሰፈርላት የቆየች ሀገር መሆኗን አንስተዋል።
ይህ ተቃርኖ መታረቅ አለበት ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፤ በሕይወት መስዋዕትነት የተገኘ ሉዓላዊነትን በላባችን ምሉዕ ማድረግ ይገባናል ብለዋል።
ኢትዮጵያ ካላት ሁሉን አቀፍ ፀጋ አኳያ የምትለምን ሳይሆን የምትሰጥ ሀገር መሆኗን ተናግረዋል።

ስንዴ የሚሰፈርለት ሀገር ነፃነት ማረጋገጥ አይችልም ያሉት አቶ ተስፋሁን፤ ያለንን ሀገራዊ ሀብት ማቀናጀትና አንገት አስደፊ የሆነውን ተረጂነት ታሪክ ማድረግ ይገባናል ነው ያሉት።
የተረጂነት ዋና ችግር የሆነው የአስተሳሰብ ችግር በመሆኑ ከአስተሳሰብ ለውጥ ጀምሮ ራስን የመቻል ጉዞ አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
በዚህም ጉዳዩን ከንቅናቄ ባሻገር መዋቅራዊና ሰው ተኮር አድርጎ መተግበር፣ የባለድርሻ አካላት ቅንጅትን ማጠናከር፣ እንደየ ዐውዱና አካባቢው ሁኔታ ለይቶ መተግበርና ቀጣይነት ያለው ተግባቦት መፍጠር ላይ በትኩረት እንዲሰራ አፅንኦት ሰጥተዋል።
ለዚህ ደግሞ የሕዝብ ለህዝብ ውይይትና የሚዲያ ይዘት ስራዎችንም በዚህ ረገድ በትኩረትና በኃላፊነት መስራት እንደሚገባ መግለጻቸዉን ኢዜአ ዘግቧል፡፡