AMN – ግንቦት 17/2018
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ጋር በመተባበር ያለማው የሃገር ውስጥ ሥራና ሠራተኛን የሚያገናኘው “ፈልጉልኝ” የተሰኘ የሞባይል መተግበሪያ ይፋ ሆኗል፡፡
በመርሐ ግብሩ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል፤ “ፈልጉልኝ” የተሰኘው የሞባይል መተግበሪያ በየአካባቢው የሚገኙ የሥራ ዕድሎችንና ሥራ የሚፈልጉ ዜጎችን በቀላሉ የሚያገናኝ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
አሰሪዎች በየአካባቢው የሚገኙ ባለሙያዎችን ልክ እንደ ‘ራይድ’ የትራንስፖርት አገልግሎት ሁሉ በዙሪያቸው ካሉበት ቦታ በመጥራት ማሰራት የሚችሉበትን ዕድል ይፈጥራልም ነው ያሉት።
መተግበሪያው በመደበኛ፣ በአጫጭር ሥልጠናዎች እንዲሁም በልምድ የተገኙ ሙያዎችን እንዳካተተ በመግለጽ ባለሙያዎች በትርፍ ሰዓት ጭምር እንዲሠሩ ዕድል ይሰጣል ማለታቸውን የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል፡፡

የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሃሚድ በበኩላቸው፤መተግበሪያው በመላው ሀገሪቱ በገጠርም ሆነ በከተማ እኩል የሚያገለግል አካታች ሥርዓት መሆኑን አንስተዋል፡፡