አሜሪካ ከአፍሪካ ጋር ያላትን የቢዝነስ ዲፕሎማሲ በአዲሱ የትራምፕ አስተዳደር ዘመን ይበልጥ ለማጠናከር እንደምትሰራ በአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የአፍሪካ ቢሮ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊ አምባሳደር ትሮይ ፊትለር ገለጹ።
አምባሳደር ትሮይ ፊትለር በአንጎላ ዋና ከተማ ሉዋንዳ እየተካሄደ ባለው የአፍሪካ አሜሪካ የቢዝነስ ጉባኤ ላይ ባደረጉት ንግግር ሀገራቸው ከአፍሪካ ጋር ያላትን የንግድና ኢንቨስትመንት ግንኙነት ለማጠናከር ትሰራለች ብለዋል።
በቅርቡም አሜሪካ አፍሪካን በተመለከተ የምትከተለው የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ የቢዝነስ ዲፕሎማሲን መሰረት እንዲያደርግ በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት በአፍሪካ የሚገኙ የአሜሪካ ኤምባሲዎች በዛው ልክ እየተንቀሰቀሱ መሆኑን አንስተዋል።
ከዚህ ጋር በተያያዘ የአሰራር ማሻሻያዎች እስከ ማድረግ የሚደርስ ውሳኔ መተላለፉን ጠቅሰዋል።
ጎን ለጎንም በንግዱ ዘርፍ በሁለቱም ወገኖች መካከል ያሉ ተዋንያኖችን ተጠቃሚ ለማድረግ በማሰብ የጋራ ገበያው ምን አይነት ለውጥ ያስፈልገዋል በሚል ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅርበት እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል።
በተለይም የንግድ ትስስሩን ለማጠናከር ከዚህ በኋላ የአሜሪካ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ወደ አፍሪካ በሚያደርጉት ጉዞ አብረዋቸው የቢዝነስ ተወካዮች በጣምራ እንዲላኩና የተለያዩ የንግድና ኢንቨስትመንት ድርድሮች እንዲያደርጉ ይደረጋልም ነው ያሉት።
በሌላ በኩል አሜሪካ በአፍሪካ በቢዝነስ ዲፕሎማሲ ማዕቀፍ በሚኖራት ተሳትፎ በተለይም በዋና ዋና የመሰረተ ልማት ግንባታ ከምታደርገው ተሳትፎ በዘለለ በዲጂታል መሰረተ ልማት ማስፋፋት ላይ ይበልጥ እንደሚሰራ ጠቅሰዋል።
ይህም አፍሪካ በዘመናዊው የዓለም የንግድ ሥርዓት ውስጥ ውጤታማ ተሳትፎ እንዲኖራት ያስችላል ብለዋል።
በጥቅሉ የአሜሪካ የንግድና ኢንቨስትመንት ሥራ ለአፍሪካ በእጅጉ ይጠቅማል ያሉት አምባሳደር ትሮይ፤ ይህ የአሜሪካ የቢዝነስ ሥራ በአመዛኙ በአዳዲስ ቴክኖሎጂና የፈጠራ ሥራ ላይ የሚያተኩር መሆኑን መናገራቸውን የኢዜአ ሪፖርተር ከስፍራው ዘግቧል።