ሰላምን ማፅናት፥ ሰላምን መንከባከብ የእያንዳንዱ ዜጋ ኃላፊነት መሆኑን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለፁ፡፡
በንድፈ ሐሳብና በመስክ የሰለጠኑ 5ኛው ኮርስ አዲስ ምልምል የሠላም ሠራዊት አባላት ተመርቀዋል። በመርሃ ግብሩ የሰላም ሰራዊትን ከህዝባችን መካከል እየመለመልን የከተማችንን ሰላም በማንኛውም እኩይ ተግባር እንዳይደናቀፍ አድርገናል ብለዋል ከንቲባ አዳነች አቤቤ።
የዛሬውን ጨምሮ 275 ሺ ተመርቀው ወደ ሥራ የገቡት የሰላም ሰራዊት አባላት ለሰላም ግንባታችን ፣ ለኢኮኖሚያችን ፈጣን ለውጥ ለማህበራዊ እንቅስቃሴ ለሚያበረክቱት አስተዋፅዖ እና አገልግሎቶች ታላቅ አክብሮት አለን ብለዋል ።

የሰላም ሰራዊቱ አባላት ጉልበታችሁን ፣ እውቀታችሁን ጊዜያችሁን በነጻ ሰጥታችሁ የምታገልናሉ ናችሁ ፣ በተሰማራችሁበት ተግባር ከሌሎችም የፀጥታ አካላት ጋር በቅንጅት በመስራት የህዝባችንን እሴቶች ጠብቃቸው የምትሰጡትን የበጎ ፈቃድ ተግባር ይበልጥ አጠናክራችሁ እንደምትቀጥሉ እምነቴ ነው ሲሉ ገልፀዋል።
አዲስ አበባ የአፍሪካ ህብረትን ጨምሮ የተለያዩ አለም አቀፍ ተቋማት መቀመጫ ፣ ዋነኛ የዲፕሎማሲ ከተማ ናት በዚህ ልክ አለም አቀፍ ተፅእኖዋን ፣ ትልቅነቷን ፣ በከፍተኛ ፍጥነት እያደገ የመጣዉን የቱሪዝም እድገት የሚመጥን ለዓለም አቀፍ ኮንፍረሶችና ስብሰባዎች ያለንን ተመራጭነት የሚያፀና በትህትና እና በፍቅር የማስተናገድ ኃላፊነታችሁን እንድትወጡ አደራ እላለሁ ሲሉ መልእክት አስተላልፈዋል ።

ጊዜው የኢትዮጵያ የማንሰራራት ጊዜ ነው ህዳሴ ግድብ ተጠናቆ ፣ በአረንጓዴ አሻራ ፣ በስንዴ ምርታማነት እና በሌሎችም መስኮች ታላላቅ ገድል ያስመዘገብንበት ወቅት ነዉ ። በቀጣይ ቀናትም በከተማችን በርካታ ዓለማቀፍ ጉባኤዎች የሚካሄድበት ነውና ለስኬታማነቱ በሃላፊነት ፣በትጋትና በትህትና አገልግሎት መስጠት ይጠበቅብናልም ሲሉ ገልፀዋል።
ሰላምን ማፅናት ፤ ሰላምን መንከባከብ የእያንዳንዱ ዜጋ ኃላፊነት ነው ያሉት ከንቲባ አዳነች አቤቤ የከተማችን ህዝብ ወትሮም ለሰላሙ ዘብ ነው ፣ ዛሬ የተመረቃችሁ የሰላም ሰራዊት አባላትም ከሰላም ወዳዱ ህዝባችሁ ጋር ሆናችሁ የከተማችንን ሰላም ለማይፈልጉ ባንዳዎችና ባዳዎች እድል ፈንታ እንዳያገኙ ኃላፊነታቸውን እንድትወጡ ሲሉ ማሳሰባቸውን ከከንቲባ ፅ/ቤት ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።