ከተሽከርካሪ የሚለቀቀውን በካይ ጋዝ ለመቀነስ ስታንዳርዱን ተግባራዊነት ለማረጋገጥ መሥራት እንደሚገባ የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ አስታወቀ።
ቢሮው ይህንን ያስታወቀው የተሽከርካሪዎች በካይ ጋዝ ለመቀነስ በወጣው መመሪያ ላይ ለሚመለከታቸው የግንዛቤ ማስጨበጫ የውይይት መድረክ ባካሄደበት ወቅት ነው።
የአዲስ አበባ ከተማ ትራንስፖርት ቢሮ ሃላፊ አቶ ያብባል አዲስ እንደተናገሩት ፣ በአዲስ አበባ በትራንስፖርት ዘርፍ የሚከሰተውን ተጽዕኖ ለመቀነስ በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል።
ከተሽከርካሪዎች የሚለቀቀውን በካይ ጋዝ ለመከላከል የተሽከርካሪ ቴክኖሎጂን ማሻሻልና ብክለቱን ለመቀነስ ትልቅ ድርሻ ያለውን የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር እንደ ሀገር እየተተገበረ ይገኛል ብለዋል።
ብክለቱን ከሚያባብሱት ጉዳዮች መካከል፣የምንጠቀመው የነዳጅ ዓይነት፣አሮጌ መኪኖች፣የትራንስፖርት ፍሰት መጨናነቅ እና የተሽከርካሪ ብዛት ዋንኞቹ ናቸው ያሉት የቢሮ ሃላፊው ይህንንም ለመከላከል መንግስት የስታንዳርድ መመሪያ ማዘጋጀቱን አመላክተዋል።
በመመሪያው መሠረትም ስታንዳርዱንም ለማስጠበቅ የሚመለከታቸው አካላት በጋራ መስራት እንዳለባቸው አሳስበዋል።
በአለሙ ኢላላ