AMN የካቲት 7/2018 ዓ.ም
የጣሊያን መፃኢ ዕድል በአፍሪካ አህጉር የወደፊት ዕጣ ፈንታ ላይ የተመሰረተ ነው ሲሉ የጣሊያን ጠቅላይ ሚኒስትር ጆርጂያ ሚሎኒ ተናገሩ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሯ ይህንን ያሉት በአዲስ አበባ እየተካሄደ ባለው 39ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ ላይ ባደረጉት ንግግር ነው::
ጠቅላይ ሚኒስትር ጆርጂያ ሚሎኒ ጣሊያን በአፍሪካ ጉዳይ አንዱ ሰጪ ሌላው ተቀባይ የሚሆንበት ግንኙነትም ሳይሆን የጋራ ብልጽግና የሚረጋገጠበት እውነተኛ ትብብር መገንባት እንደምትፈልግ ገልጸዋል፡፡
ለዚህም ሀገራቸው ጣሊያን በሀይል አቅርቦት፣ ግብርና፣ ውሃ፣ ጤናና ትምህርት ዘርፎች ላይ ትኩረት የሚያደርገው የማቲ ዕቅድ እየተገበረች መሆኑን አስታውቀዋል።
የጣሊያን እና አፍሪካ ትብብርን የሚያጠናክረው የማቲ ዕቅድ የፕሮጀክቶች ስብስብ ብቻ ሳይሆን የትኛውም የወደፊት የተባበረና የልማት ሞዴል ያለ አፍሪካ ማሰብ እንደማይቻል ማሳያ ነው ብለዋል፡
ለዚህም የጣሊያን ተቋማት፣ ኩባንያዎች፣ ዩኒቨርሲቲዎች እና ተመራማሪዎች በአፍሪካ በጋራ ይሰራሉ ብለዋል፡፡
እንዲሁም ጣሊያን አጀንዳ 2063 ለማሳካት ከአፍሪካ ሕብረት ጎን እንደምትቆም በንግግራቸው አረጋግጠዋል፡፡
ሁለተኛው የጣሊያን-አፍሪካ ስብሰባ በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከለ በትላንትናው ዕለት መካሄዱ ይታወሳል፡፡
በትዝታ መንግስቱ