AMN ሚያዝያ 11/2018
የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ የተመዘገቡ የሪፎርም እና የልማት ስኬቶችን ለማስቀጠል የሚያደርገውን ድጋፍ ይበልጥ እንደሚያሳድግ አስታወቀ።
የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) እና የዓለም ባንክ ዓመታዊ የፀደይ ወቅት ስብሰባ በዋሺንግተን ዲሲ እየተካሄደ ነው።
በገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ የተመራ የኢትዮጵያ ልዑክ ከስብሰባው ጎን ለጎን፣ከዓለም ባንክ የኦፕሬሽን ማኔጂንግ ዳይሬክተር አና ቤርዴ ጋር ውይይት አድርጓል።
ሚኒስትር አህመድ ሽዴ የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ሪፎርም ሂደትና እያጋጠሙ ያሉ ዓለም አቀፋዊ ተጽዕኖዎችን በዝርዝር ያቀረቡ ሲሆን፤የልማት ስኬቶችን ዘላቂ ለማድረግ የዓለም ባንክ ድጋፉን እንዲያጠናክር ጠይቀዋል።
ሚኒስትሩ የዓለም ባንክ የፋይናንስ አቅርቦቱን እንዲያሰፋና ፈጣን ምላሽ የሚሰጥ የድጋፍ ማዕቀፍ እንዲዘረጋ ጠይቀዋል።
የማክሮ ኢኮኖሚ መረጋጋትን ለማረጋገጥ በኢትዮጵያ መንግሥት፣በዓለም ባንክና በአይኤምኤፍ መካከል የተቀናጀ የድጋፍ ጥቅል ማሰባሰብ በሚቻልበት ሁኔታ ላይም ምክክር ተደርጓል።
የዓለም ባንክ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አና ቤርዴ በበኩላቸው፣የዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ ያለውን ጽኑ አጋርነት ያረጋገጡ ሲሆን፤ በዚህ ወሳኝ ወቅት ከልማት አጋሮች ጋር በመቀናጀት ተቋሙ ድጋፉን ይበልጥ ለማሳደግ ዝግጁ መሆኑን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ልዑክ በዕዳ ሽግሽግ ሂደቱ የተመዘገቡ ስኬቶችን አስመልክቶ ማብራሪያ የሰጠ ሲሆን፤ የዕዳ ዘላቂነትን ለማረጋገጥ ከግል አበዳሪዎች ጋር እየተደረገ ያለው ውይይት ውጤታማ መሆኑን ገልጿል።
በተጨማሪም ሁለቱ ወገኖች በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያንን የኃይል ተጠቃሚ የሚያደርገውንና የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ሽግግር የማፋጠን አላማ ያለውን “Mission 300” የተሰኘ የኤሌክትሪክ ተደራሽነት መርሃ ግብር ተፈጻሚነት ለማጠናከር እንደሚሰሩ ገልጸዋል።
ሁለቱ ወገኖች ለቀውሶች ፈጣን ምላሽ የሚሰጡ ድጋፎችን ለማቀላጠፍና ለኢትዮጵያ ሕዝብ ተጨባጭ የልማት ውጤቶችን ለማምጣት በጋራ ለመሥራት ጽኑ ቁርጠኝነት መግለጻቸውን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኤኤምኤን በላከው መረጃ አስታውቋል።