AMN – ሐምሌ 14/2018 ዓ.ም
የኮይሻ የኃይል ማመንጫ ቤት የመጀመሪያ ምዕራፍ የስትራክቸራል ኮንክሪት ሙሌት ሥራ መጠናቀቁን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አስታወቀ።
የኮይሻ የኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት የሲቪል መሐንዲስ አቶ ይታገሱ አያሌው እንደተናገሩት ፣ ፕሮጀክቱ በኢትዮጵያ የኃይል ልማት ዘርፍ ከታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ እና ከጊቤ 3 የኃይል ማመንጫ ጣቢያዎች ቀጥሎ 3ኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ነው።
የግድቡ የአርማታ ሙሌት ግንባታ ከመከናወኑ በፊት ከ7 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ ልል አፈር የማንሳት ሥራ መሰራቱን ተናግረዋል።

በአሁኑ ወቅት ከ7 ነጥብ 725 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ የአርማታ ሙሌት ውስጥ ከ6 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ የአርማታ ጥቅጥቅ ሙሌት መጠናቀቁም ተገልጿል።
ግንባታውን ለማፋጠን በ2 ፈረቃ ለ24 ሰዓታት እየተሰራ መሆኑን የገለፁት አቶ ይታገሱ በየወሩ በአማካኝ ከ100 ሺህ ሜትር ኪዩብ በላይ የአርማታ ጥቅጥቅ ሙሌት እየተከናወነ እንደሚገኝ መናገራቸውን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ባወጣው መረጃ ጠቅሷል።