AMN – መጋቢት 9/2017 ዓ.ም
ዕምቅ የፈጠራ አቅምና ችሎታ ያላቸው ታዳጊዎችን ለማፍራት አዳዲስ መርሐ ግብሮች ወደ ተግባር መግባታቸውን የስራና ክህሎት ሚኒስቴር ገለፀ።
ሚኒስቴሩ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር “ብሩህ እናት” የተሰኘ የሴት ኢኖቬተሮች የፈጠራ ሃሳብ ውድድር የቡት ካምፕ ስልጠና ማስጀመሪያ መርሃ ግብር አካሂዷል።
የስራና ክህሎት ሚንስትር ዴኤታ አቶ ሰለሞን ሶካ በወቅቱ እንዳሉት፣ የኢትዮጵያን የብልጽግና ጉዞ ለማሳካት የቴክኖሎጂ ሽግግር ማድረግ አስፈላጊ ነው።
ለዚህም የስራና ክህሎት ሚኒስቴር አዳዲስ ቴክኖሎጂ የሚያመነጩና የፈጠራ ሃሳብ ያላቸውን ወጣቶች የሚደግፉ መርሐ ግብሮችን እየቀረጸ መሆኑን ጠቅሰዋል።
ይህንንም ተከትሎ አዳዲስ አሰራሮችን ተግባራዊ በማድረግ እምቅ አቅምና ችሎታ ያላቸውን ታዳጊዎችና ወጣቶች ለማፍራት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
ከዚህም በተጨማሪ ችግር ፈቺ የፈጠራ ሃሳብ ያላቸው ዜጎች ሃሳባቸው ወደ ተግባር ተቀይሮ ተጨባጭ ውጤት እንዲያስገኝ ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል፡፡
በዚህ ረገድ አዳዲስ ቴክኖሎጂ የሚያመነጩና የፈጠራ ሃሳብ ያላቸውን ወጣቶች የሚደግፉ ፕሮግራሞች በመቅረፅ ተግባራዊ እየተደረጉ ነው ብለዋል፡፡
“ማሰልጠን፣ መሸለም እና ማብቃት” በሚል መሪ ሀሳብ የሚካሄደው “ብሩህ ኢትዮጵያ” ሀገር አቀፍ የቢዝነስ ፈጠራ ሃሳብ ውድድር ከእነዚህ ፕሮግራሞች መካከል አንዱ መሆኑን አንስተዋል፡፡
በመርሐ ግብሩ በውድድር ያለፉ 50 የፈጠራ ሀሳብ ያላቸው ሴቶች ተጨማሪ ስልጠና እንደሚወስዱ መጥቀሳቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
ከስልጠና በኋላ በውድድሩ ለሚያሸንፉ 10 ምርጦች ከመቶ ሺህ እስከ ግማሽ ሚሊዮን ብር ሽልማት እንደሚሰጣቸው አመላክተዋል፡፡