ኢሬቻ በዓል ባህላዊ እሴቱን ጠብቆ በደመቀና ባማረ መልኩ እንዲከበር በማድረግ ለቱሪዝም ፍሰት የሚያበረክተውን ጉልህ አስተዋጽኦ ማሳደግ እንደሚገባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገልፀዋል፡፡
አባገዳዎች ፣ ሃደስንቄዎች ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች ጋር የኢሬቻ በዓል እሴቱን ጠብቆ ለማክበር በተካሄዱ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች ላይ ተወያይተዋል።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ፤ የኢሬቻ በዓል ሲከበር በርካታ የሃገር ውስጥና የውጭ ሃገራት ዜጎች ጭምር የሚሳተፉበት ክብረ-በዓል በመሆኑ ባህላዊ እሴቱን ጠብቆ በደመቀና ባማረ መልኩ እንዲከበር በማድረግ ለቱሪዝም ፍሰት የሚያበረክተውን ጉልህ አስተዋጽኦ ይበልጥ ማሳደግ ይገባል ብለዋል።

የኢሬቻ በዓል የኦሮሞ ህዝብ ለፈጣሪው ምስጋና የሚያቀርብበት ፤ የሰላም ፣ የእርቅ እና የወንድማማችነት የአደባባይ ክብረ-በዓል መሆኑን ገልጸው ባህላዊ እሴቱን ጠብቆ ሰላማዊ ሆኖ እንዲከበር በርካታ ዝግጅት መደረጉን አባገዳዎች ገልፀዋል፡፡
ኢሬቻ ከፍተኛ የቱሪዝም ገቢ ማስገኛ በዓል ሆኗል ያሉት ተወያዮቹ፤ በዓሉ ከፍተኛ የባህላዊ አልባሳት እና የሆቴሎች አገልግሎት ግብይት የሚካሄድበት በመሆኑ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ሰፊ ዝግጅት እንዲያደርጉም ጠይቀዋል።
አያይዘዉም በኮሪደር ልማትና በወንዝ ዳርቻ ልማት እየተገነቡ ያሉ የልማት ስራዎች ለአደባባይ በዓላት ምቹ ሁኔታን ፈጥረዋል ያሉት አባገዳዎች ፤ ከአደባባይ በዓላት መካከል አንዱ የሆነውን የኢሬቻን ክብረ በዓል በደመቀ መልኩ እንዲከበር የከተማ አስተዳደሩ ለሚያደርገው ድጋፍ ምስጋናቸዉን ማቅረባቸውን ከከንቲባ ጽ/ቤት ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡
የዘንድሮዉ አመት የኢሬቻ ክብረ በአል “ኢሬቻ ለሀገር ማንሰራራት “ በሚል መሪ ቃል የሚከበር ይሆናል።