ሀገራችን ፈተናዎችን በድል እየተሻገረች ሁሌም አሸናፊ ሆና እንድትቀጥል ሕብረ ብሔራዊ አንድነትን ማጠናከር እና እውነተኛ የፌደራል ስርዓት መገንባት እንደሚያስፈልግ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አቶ አገኘሁ ተሻገር ገለጹ፡፡
አቶ አገኘሁ ተሻገር 20ኛው የኢትዮጵያ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን በተከበረበት ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በሆሳዕና ከተማ በመገኘት ንግግር አድርገዋል፡፡
አፈ ጉባዔው እውነተኛ የፌደራል ስርዓት ሁሉንም ማንነቶች የማስተናገድ አቅም እና ፍላጎት እንዳለው በመግለጽ የሕዝቦችን አንድነት እና ትስስር ለማረጋገጥ እንዲሁም የሀገራችንን ሰላም እና አንድነት ጠብቆ ለማቆየት ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባም አሳስበዋል፡፡
ኢትዮጵያ በለውጡ መንግሥት አመራር ወደሚገባት ከፍታ ለመውጣት የማንሠራራት ጉዞዋን አስቀጥላ የማይቻል የሚመስሉትን ችላ አሳይታለች ያሉት አቶ አገኘሁ ተሻገር እነዚህ ሁሉ የተሳኩት ስለተባበርን ነው በማለት ገልጸዋል፡፡
ጥረቶቻችን በውጤት እና በስኬት የሚጠናቀቁት በሁለንተናዊ መልኩ ስንተባበር፣ ሀሳብ ስናዋጣ እና በአንድነት ስንቆም ብቻ መሆኑን አፈ ጉባዔው ተናግረዋል፡፡
አፈጉባዔው ሁሉም የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በተሰማሩበት ሞያ በሚችሉት አቅም ለሀገራቸው ከፍታ እና የለውጥ ጉዞ የበኩላቸውን እንዲወጡ ቃልኪዳናቸውንም እንዲያድሱ ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡