ድርጅቱ በ2018 በጀት አመት በቀን በአማካይ 1 ነጥብ 3 ሚሊዮን ተገልጋዮችን አጓጉዟል

You are currently viewing ድርጅቱ በ2018 በጀት አመት በቀን በአማካይ 1 ነጥብ 3 ሚሊዮን ተገልጋዮችን አጓጉዟል

AMN – ሐምሌ 14/2018 ዓ.ም

የአዲስ አበባ ከተማ አውቶቡስ አገልግሎት ድርጅት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ካቀዳቸው ዋና ዋና ግቦች ውስጥ 98 በመቶ ማሳካቱን ገልጿል፡፡

ከኤ ኤም ኤን ጋር ቆይታ ያደረጉት የአዲስ አበባ የከተማ አውቶቡስ አገልግሎት ድርጅት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ አካሉ አሰፋ ድርጅቱ በቀን በአማካይ 1 ነጥብ 3 ሚሊዮን ተገልጋዮችን ማጓጓዝ መቻሉን አስታውቀዋል።

ድርጅቱ ከዚህ ቀደም ይገጥሙት የነበሩትን የአገልግሎት አሰጣጥ፣ የአሰራርና የአደረጃጀት ችግሮች ለመቅረፍ በተደረገው ልዩ የሪፎርም ሥራ ከፍተኛ ለውጥ ማስመዝገብ መቻሉን ገልጸዋል።

ተቋሙ ቀደም ሲል በነበሩት አሰራሮችና የአገልግሎት መቆራረጦች ምክንያት የሕዝብ ቅሬታ ይነሳበት እንደነበር ያብራሩት አቶ አካሉ፣ በከተማ አስተዳደሩ በተደረገለት ልዩ ድጋፍ ከ12 በላይ አዳዲስ መመሪያዎችና አሰራሮች ተዘጋጅተው ወደ ሥራ መግባታቸውን ጠቁመዋል።

በተጨማሪም አሰራሩን በቴክኖሎጂ በማስደገፍና ተገቢውን የሰው ኃይል በቦታው በመመደብ የአገልግሎት አሰጣጡን ውጤታማ ማድረግ ተችሏል ብለዋል።

ድርጅቱ በበጀት ዓመቱ በቀን ያጓጉዘው የነበረውን የሕዝብ ቁጥር ከ1 ነጥብ 1 ሚሊዮን ወደ 1 ነጥብ 3 ሚሊዮን ከፍ ማድረግ የቻለ ሲሆን፣ የዕቅድ አፈጻጸም ምጣኔውም ከነበረበት 96 በመቶ ወደ 98 በመቶ ማደጉን አስረድተዋል።

በበጀት ዓመቱ ካጋጠሙ ዋና ዋና ተግዳሮቶች መካከል ከውጭ በሚገቡ የመለዋወጫ ዕቃዎች አቅርቦት ላይ የነበረው እጥረትና የዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ እንደሚገኙበት የተናገሩት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ እነዚህን ችግሮች ለመቋቋም በውስጥ ባለሙያዎች የፈጠራ ሥራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል።

ለአብነት ያህል በገበያ ላይ በቀላሉ ማግኘት ያልተቻሉ የውኃ ፓምፖችን በውስጥ ባለሙያዎች ማሻሻል በመቻሉ፣ ከ50 በላይ አውቶቡሶች ከሥራ ውጪ እንዳይሆኑ ማድረግ መቻሉንና በዚህም ከ10 ሚሊዮን ብር በላይ ማዳን መቻሉን አብራርተዋል።

የከተማዋን ፈጣን እድገትና እየጨመረ የመጣውን የትራንስፖርት ፍላጎት ለማሟላት ድርጅቱ የረጅም ጊዜ መፍትሔዎችን በማዘጋጀት ላይ መሆኑን አቶ አካሉ ገልጸዋል።

የመንግሥትን የነዳጅ ድጎማ ጫና ለመቀነስና ለአካባቢ ተስማሚ የሆነ አገልግሎት ለመስጠትም የከተማ አስተዳደሩ አዳዲስ የኤሌክትሪክ አውቶቡሶችን እያስገባ ይገኛል።

በሚቀጥለው የበጀት ዓመት የኤሌክትሪክና አውቶቡሶችን ቁጥር በመጨመር፣ የጥገና አቅምን በማሳደግና የአገልግሎት መስመሮችን በማስፋፋት ይበልጥ ደህንነቱ የተጠበቀና ፈጣን የትራንስፖርት አገልግሎት ለመስጠት ዝግጅት መደረጉን ዋና ሥራ አስፈጻሚው አረጋግጠዋል።

በወርቅነህ አቢዮ

0 Reviews ( 0 out of 0 )

Write a Review