AMN – ግንቦት 09/2018 ዓ.ም
ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ሊካሄድ ጥቂት ቀናት ብቻ ቀርተውታል። የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ባስቀመጠው የጊዜ ገደብ መሠረት ህዝቡ የምርጫ ካርዱን ወስዷል።
የአዲስ አበባ ነዋሪዎችም የምርጫ ካርዳቸውን በመያዝ የምርጫ ቀኑን በጉጉት እየተጠባበቁ መሆናቸውን ለኤኤምኤን በሰጡት አስተያየት ገልጸዋል።
አቶ ኤፌሶን ቶማ በሰጡት አስተያየት ምርጫ ካርድ መውሰዳቸውን ገልጸው ፣ የፓርቲዎች ሀሳብ፣ እቅድና አላማ እየተከታተሉ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
ለሀገሪቷ ለህዝቡና ለወጣቱ ነገ የተሻለ ተስፋ ያለውን ፓርቲ ለመምረጥ ቀኑን በመጠባበቅ ላይ ነኝ ብለዋል።

ታምራት አዲስ በበኩላቸው ጠዋት ሄጄ ሰዓቴን ጠብቄ ለመምረጥ ዝግጁ ነኝ ሲሉ የምርጫውን እለት በጉጉት እንደሚጠባበቁ ተናግረዋል።
ሳራ በላይነህ እና ሰለሞን ሞገስ በበኩላቸው የዜግነት ግዴታቸውን ለመወጣት ካርዳቸውን ቀድመው መውሰዳቸውን ገልጸዋል። ይበጀኛል የሚሉትን ፓርቲ ለመምረጥ መዘጋጀታቸውንም ጠቁመዋል።
አስተያየት ሰጪዎቹ አክለውም፣ የምርጫ ካርድ የወሰደ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ይበጀኛል ያለውን ፓርቲ በመምረጥ የወሰደውን ካርድ ለታለመለት ሀገራዊ አላማ ማዋል እንዳለበት አሳስበዋል።

ምርጫ ለሀገር ህልውና እና ለዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ትልቅ ፋይዳ እንዳለው ነው ነዋሪዎቹ የገለጹት።
ኤፌሶን ቶማ ሁሉም ዜጋ በነቂስ ወጥቶ መምረጥ አለበት ምክንያቱም መንግስት ሲኖር ነው አንድ ሀገር የተረጋጋ ሰላም፣ የተረጋጋ ኢኮኖሚና ልማት ሊኖረው የሚችለው ሲሉ አስገንዝበዋል።